Popular Posts

Saturday, October 28, 2017

ዘይት መሸጥ ችግሩ ምንድነው ?

ኢየሱስን የምንከተል ሁላችን ከተባረክናባቸው በረከቶች አንዱ የስጋ ፈውስ ነው፡፡ እግዚአብሄር በክርስቶስ በኩል የሃጢያታችንን እዳ እንደከፈለና ነፍሳችን ከሃጢያት ነፃ እንዳወጣ ሁሉ እንዲሁ ኢየሱስ በመገረፉና ለስጋችን ፈውስና ጤንነት ሙሉ ዋጋ በመክፈሉ ፈውስ የእኛ ነው፡፡
ስለዚህ ነው የቤተክርስቲያን ሽማግሌዎች በታመመ ሰው ላይ ዘይትት ቀብተው እንዲፀልዩለት መፅሃፍ ቅዱስ የሚያስተምረው፡፡
የቤተክርስትያን ሽማግሌዎች ሃላፊነት በቤተክርስትያናቸው ስለፈውስ ማስተማር ነው፡፡ የእግዚአብሄርን ቃል ስናስተምር የእግዚአብሄ ህዝብ እግዚአብሄር ለእርሱ ያለውን የፈውስ አላማ ሲረዳ ይፈወሳል፡፡ እምነት የእግዚአብሄርን ቃል ከመስማት ይመጣልና፡፡  
እንግዲያስ እምነት ከመስማት ነው መስማትም በእግዚአብሔር ቃል ነው። ሮሜ 1017
የቤተክርስትያን ሽማግሌዎች በግልፅ እንደተፃፈው የእግዚአብሄር ቃል ትእዛዝ ለታመመ ሰው ዘይት ቀብተው መፀለይ ነው፡፡ ሽማግሌዎች በታመመ ላይ ዘይት ቀብተው በመፀለይ የእግዚአብሄርን ቃል መታዘዝ አለባቸው፡፡  
ከእናንተ የታመመ ማንም ቢኖር የቤተ ክርስቲያንን ሽምግሌዎች ወደ እርሱ ይጥራ፤ በጌታም ስም እርሱን ዘይት ቀብተው ይጸልዩለት። ያዕቆብ 5፡14
ያም ሆነ ይህ የእምነት ፀሎት ነው በሽተኛውን የሚፈውሰው፡፡ ሰው እግዚአብሄር ስለእርሱ ያለውን የፈውስ አላማ ከእግዚአብሄር ቃል ሰምቶ ሲያምን ይፈወሳል፡፡ ሐዋርያት 14፡9
ይህም ሰው ጳውሎስ ሲናገር ይሰማ ነበር፤ እርሱም ትኵር ብሎ ተመለከተውና ይድን ዘንድ እምነት እንዳለው ባየ ጊዜ፥
ሰወ የእግዚአብሄርን ቃል ሲሰማ እምነት ይኖረዋል፡፡ እምነት ሲኖረው እምነቱ ይፈውሰዋል፡፡
እርሱም፦ ልጄ ሆይ፥ እምነትሽ አድኖሻል፤ በሰላም ሂጂ ከሥቃይሽም ተፈወሽ አላት። ማርቆስ 5፡34
አንዳንድ አገልጋዮች ዘይት ቀብተው ለበሽተኞች ይፀልያሉ፡፡ ዘይቱን ወደቤቱ ወስፈዶ መፀለይ ለሚፈልግ ሰው ዘይትን ይሰጣሉ ወይም ይሸጣሉ፡፡ አንዳንድ ሰው ዘይቱን የሚገዛው መምጣት ላልቻለ ለታመመ ሰው ላይ ወስዶ ለመፀለይ ነው፡፡
ድውዮችን ፈውሱ፤ ሙታንን አስነሡ፤ ለምጻሞችን አንጹ፤ አጋንንትን አውጡ፤ በከንቱ ተቀበላችሁ፥ በከንቱ ስጡ። ማቴዎስ 10፡8
ዘይቱን ስለመሸጥ ስናስብ የመሸጥ ችግሩ ምንድነው ዘይት ብለን እንደ እግዚአብሄር ቃል ማሰብ ይኖርብናል፡፡ ዘይት ገዝተው በሰው ላይ ለመቀባትና ለመፀለይ ወይም በራሳቸው ላይ ለመቀባትና ለመፀለይ ለሚፈልጉ ሰዎች ዘይቱን መሸጥ ችግሩ ምንድነው የሚለውን ጥያቄ መመለስ በጣም አስፈላጊ ነው፡፡
በደንብ ብናስበው ዘይቱ የሚገኘው በገንዘብ ነው፡፡ ትንሽም ቢሆን ማሸጊያና ሌሎች ወጭዎች ይኖሩታል፡፡ ያንን ወጪ ማን ይሸፍን ነው ጥያቄው? አገልጋዩ ያንን ወጭ ሸፍኖ በነፃ መስጠት ቢችል እሰየው ነው፡፡ ካልቻለ ግን ዘይቱን ለመግዛትና ለማሸግ ያወጣውን ወጭ ቢመልስ ችግሩ ምንድነው? ሰው በዘይቱ ከሚያገኘው መንፈሳዊ ጥቅም አንፃር የዘይቱን መጋና´ማሸጊያ ለጥቃቅን ወጪዎችን ቢከፍል ትልቅ ነገር ነውን?
እኛ መንፈሳዊን ነገር የዘራንላችሁ ከሆንን የእናንተን የሥጋዊን ነገር እኛ ብናጭድ ትልቅ ነገር ነውን? 1ኛ ቆሮንቶስ 9፡11
እውነት ነው ፀጋው ነፃ ነው፡፡ የፈውስ ስጦታው ነፃ ነው፡፡ ነገር ግን ዘይቱን ለመግዛትና ለማሸግ ነፃ አይደለም ገንዘብ ያስወጣል፡፡
በቅንነት ካየነው አገልጋዮች ለዘይቱና ለማሸጊያው ያወጡትን ተመጣጣኝ ዋጋ ቢመልሱ ምንም ችግር የለበትም፡፡
ይህ ማለት አገልጋዩ ስስታም አይሆንም ማለት አይደለም፡፡ ይህ ማለት አገልጋዩ በዚያ አጋጣሚ ተጠቅሞ ብዙ ገንዘብ ለማግኘት አይሞክርም እያልኩ አይደለም፡፡ አገልጋዩ ራስ ወዳድ ሊሆንና ከሰዎች መፈወስ በላይ የራሱን ጥቅም ሊያስቀድምና ካለምንም ምክኒያት ካወጣው ወጭ በላይ ብዙ እጥፍ ሊያስከፍል ይችላል፡፡ ይህ በፍፁም ተቀባይነት የሌለው ነገር ነው፡፡ ሰው ለዘይቱና ለማሸጊያው ያወጣውን ወጭ አስታኮ በነፃ የተቀበለውን የእግዚአብሄርን ነገር መሸጥ ስግብግብነት ነው፡፡
ኢየሱስን በግልፅ የተቃወመው መንፈሳዊ ነገርን ፈልገው የመጡ ሰዎችን ላይ አላግባብ መጠቀምን ነው፡፡
እናንተ ግብዞች ጻፎችና ፈሪሳውያን፥ በጸሎት ርዝመት እያመካኛችሁ የመበለቶችን ቤት ስለምትበሉ፥ ወዮላችሁ፤ ስለዚህ የባሰ ፍርድ ትቀበላላችሁ። ማቴዎስ 23፡14
የእግዚአብሄርን ፈውስ ፈልገው የመጡን ሰዎች ይህን ያህል ገንዘብ ካልከፈላችሁ ብሎ የተጋነነ ገንዘብ መጠየቅና ማስጨነቅ ስጋዊነት ነው፡፡
በመጀመሪያይቱም ቤተክርስትያን መንፈስ ቅዱስን ለመሙላት ለሃዋሪያት ብር ሊሰጣቸው የሞከረውን ሰው ሃዋሪያት አጠንክረው ሲገስፁት እንመለከታለን፡፡ የእግዚአብሄርን ስጦታ በገንዘብ መቸርቸር በነፃ ተቀብላችሁዋልና በነፃ ስጡ የሚለው መፅሃፍ ቅዱሳዊ መርህ ይቃወማልና፡፡
ሲሞንም በሐዋርያት እጅ መጫን መንፈስ ቅዱስ እንዲሰጥ ባየ ጊዜ፥ ገንዘብ አመጣላቸውና። እጄን የምጭንበት ሁሉ መንፈስ ቅዱስን ይቀበል ዘንድ ለእኔ ደግሞ ይህን ሥልጣን ስጡኝ አለ። ጴጥሮስ ግን እንዲህ አለው፦ የእግዚአብሔርን ስጦታ በገንዘብ እንድታገኝ አስበሃልና ብርህ ከአንተ ጋር ይጥፋ። ሐዋርያት 8፡18-20
አገልጋዮች ስለኑሮዋቸው በእግዚአብሄርን መታመን አለባቸው፡፡ እግዚአብሄር የሰጣቸውን ነፃ ስጦታ በነፃ መስጠት አለባቸው፡፡ አገልጋዮች እግዚአብሄር የሰጣቸው ስጦታ ብዙ ገንዘብ ማግኛ መንገድ ለማድረግ ያለባቸውን ስጋዊ ፈተና ማሸነፍ እግዚአብሄን በስኬት እንዲየገለግሉት ያስችላቸዋል፡፡ አገልጋዮች የእግዚአብሄር ህዝብ መባረክ ፣ መጠቀምና መፈወስ ላይ ማተኮር አለባቸው፡፡ አገልጋዮች የእግዚአብሄርን መንግስትና ፅድቁን ሲፈልጉ እግዚአብሄር ደግሞ የሚያስፈልጋቸውን ሁሉ አንደሚያሟላላቸው በእግዚአብሄር መታመን አለባቸው፡፡
እንግዲህ፦ ምን እንበላለን? ምንስ እንጠጣለን? ምንስ እንለብሳለን? ብላችሁ አትጨነቁ፤ ይህንስ ሁሉ አሕዛብ ይፈልጋሉ፤ ይህ ሁሉ እንዲያስፈልጋችሁ የሰማዩ አባታችሁ ያውቃልና። ነገር ግን አስቀድማችሁ የእግዚአብሔርን መንግሥት ጽድቁንም ፈልጉ፥ ይህም ሁሉ ይጨመርላችኋል። ማቴዎስ 6፡ 31-33  
ለተጨማሪ ፅሁፎች https://www.facebook.com/abiy.wakuma/notes
ለቪዲዮ መልእክቶች https://www.youtube.com/user/awordm/videos

#ፈውስ #እምነት #ቁስል #ህመም #ደዌ #ጤንነት #በነፃ #ዘይት #ቅባት #አማርኛ #ስብከት #መዳን #መፅሃፍቅዱስ #መንፈስቅዱስ #በመገረፉ #ፌስቡክ #አቢይዋቁማ #አቢይዋቁማዲንሳ  

No comments:

Post a Comment