Popular Posts

Tuesday, October 24, 2017

እሳትን የሚያጠፉ አራት ነገሮች

በምድር ላይ የእግዚአብሄርን ፈቃድ በትጋትና በድፍረት ፈፅመን እንድናልፍ ከሚያግዙ ነገሮች አንዱ ግለት እሳትና መቀጣጠል ነው፡፡ ሰው በምድር ላይ የእግዚአብሄርን ፈቃድ የሚፈፅምበት እምቅ ጉልበት ኖሮት እሳቱና ግለቱ ከውስጡ ከጠፋ ለምንም አይጠቅምም፡፡ ሰው የእግዚአብሄርን ፈቃድ ለመፈፀም ረሃቡና ጥማቱ ያስፈልገዋል፡፡ እግዚአብሄር በህይወቱ ያየውን ነገር ለማግኘት ቅናት ይጠይቃል፡፡ ሰው ግን ግድ የለሽና ልቡ ሙትት ያለ ከሆነ የእግዚአብሄን ፈቃድ መፈፀም አይችልም፡፡  
እሳትና ግለት ጉልበትን ይሰጠናል እሳትና መቀጣጠል ቅናት የምድር አስቸጋሪ ሁኔዎችን አልፈን እንድንሄድ ያስችለናል፡፡ ሃሞቱ ከፈሰሰ ግን አንዳች ማድረግ ያቅተናል፡፡
የእግዚአብሄርን ነገር ለመጨበጥ ረሀቡና ጥማቱ ከሌለ በውስጣችን የሚወለድ ብዙ ነገር እያለ የትም መድረስ ያቅተናል፡፡   
እነርሱም፦ ሕዝቅያስ እንዲህ ይላል፦ ይህ ቀን የመከራና የተግሣጽ የዘለፋም ቀን ነው፤ ልጆች የሚወለዱበት ጊዜ ደርሶአል ለመውለድም ኃይል የለም። ኢሳይያስ 37፡3
እግዚአብሄር ለብዙ ነገር አስቦንም እያለ መራመድ ያቅታል፡፡ እግዚአብሄር ከፍ ላለ ነገር ጠርቶን እያለ ጉልበት ያጥራል፡፡
ወንድሞች ሆይ፥ እኔ ገና እንዳልያዝሁት እቈጥራለሁ፤ ነገር ግን አንድ ነገር አደርጋለሁ፤ በኋላዬ ያለውን እየረሳሁ በፊቴ ያለውን ለመያዝ እዘረጋለሁ፥ በክርስቶስ ኢየሱስ ከፍ ከፍ ያለውን የእግዚአብሔርን መጥራት ዋጋ እንዳገኝ ምልክትን እፈጥናለሁ። ፊልጵስዩስ 3፡13-14
እግዚአብሄር እስራኤልን ሊያስወርስ ያለው ብዙ ምድር እያለ ኢያሱ ግን አረጀ፡፡ ልቡ እንዳረጀበት ሰው አቅሙ ሁሉ እያለውቅ ነገር ግን ምንም ማድረግ የማይችል ሰው የለም፡፡
ኢያሱም ሸመገለ በዕድሜም አረጀ እግዚአብሔርም አለው፦ አንተ ሸመገልህ፥ በዕድሜህም አረጀህ፤ ያልተወረሰች እጅግ ብዙ ምድር ገና ቀርታለች፤ ኢያሱ 13፡1
ካሌብ በሰማኒያ አመቱ ትኩስ ነበር፡፡ ሊወርስ ሊወስድ ሊዋጋ እና ሊወጣ የተዘጋጀ ነበር፡፡
ሙሴም በላከኝ ጊዜ እንደ ነበርሁ፥ ዛሬ ጕልበታም ነኝ፤ ጕልበቴም በዚያን ጊዜ እንደ ነበረ፥ እንዲሁ ዛሬ ለመዋጋት ለመውጣትም ለመግባትም ጉልበቴ ያው ነው። ኢያሱ 14፡11
እግዚአብሄን በሃይል ሲያገለግል የነበረው ታላቁ ነቢይ ኤልያስ አንድ ጊዜ ጉልበት አጠረው፡፡ እግዚአብሄር ሊሰራበት ያለው ብዙ ነገር እያለ ልቡ ተሸነፈ እኔ በቃኝ አለ፡፡
እርሱም አንድ ቀን የሚያህል መንገድ በምድረ በዳ ሄደ፤ መጥቶም ከክትክታ ዛፍ በታች ተቀመጠና፦ ይበቃኛል አሁንም፥ አቤቱ፥ እኔ ከአባቶቼ አልበልጥምና ነፍሴን ውሰድ ብሎ እንዲሞት ለመነ። 1ኛ ነገሥት 19፡4
የእግዚአብሄን ህዝብ ለመባረክ ለበረከት ለመሆን አቅሙ ሁሉ እያለን የምንቆመው እሳታችንን ከውስጣችን ሲጠፋ ብቻ ነው፡፡ እሳታችን ከጠበቅን እርምጃችንንና ፍጥነታችን መጠበቅ እንችላለን፡፡ በምንም ሁኔታ ሊያቆመን አይችልም፡፡ ድፍተራችን ከተመታ ግን ምንም ምክኒያት ሊያስቆመን ይችላል፡፡  
ብዙ ነገሮችን ለጌታ የማድረግ እምቅ ጉልበት እያለን እሳታችንን የሚበላውና ለእግዚአብሄር የመሮጥና ሃሞታችን የሚፈሰው ምን እንደሆነ እንመልከት፡፡  
1.      የሰው የንቀት እይታ
ካለተጠነቀቅን የሰው እይታ እና የሰው አስተያየትን ጉልበታችንን ይበላል፡፡ እንዳንወጣ እንዳንወርስ ጌታ ለጠራን ጥሪ እንዳንዘረጋ ያደርጋል፡፡
ዳዊት የወንድሞቹን ንቀት ቢያምን ኖሮ ታሪክን አይሰራም ነበር፡፡ እኛም በክርስቶስ ያለንበትን ስፍራ ከላየን በስተቀር ምንም ማድረግ የማንችል ከንቱ ሆነን እንቀራለን፡፡
ታላቅ ወንድሙም ኤልያብ ከሰዎች ጋር ሲነጋገር ሰማ፤ የኤልያብም ቍጣ በዳዊት ላይ ነድዶ፦ ለምን ወደዚህ ወረድህ? እነዚያንስ ጥቂቶች በጎች በምድረ በዳ ለማን ተውሃቸው? እኔ ኵራትህንና የልብህን ክፋት አውቃለሁና ሰልፉን ለማየት መጥተሃል አለው። 1ኛ ሳሙኤል 17፡28
ለአንዳንድ ሰው ምንም ብታደርጉ በቂ አይደለም፡፡ አንዳንደ ሰው ምንም ብትሆኑ አይቀበላችሁም፡፡ የሰውን ንቀት ሰምተን ከቆምን ለምንም አንሆንም፡፡
2.     የእግዚአብሄር ቃል እጦት
የእግዚአብሄር ቃል በእምነት እንዴት እንደምንንራመድ ምሳሌዎችን እየጠቀሰ ያስተምረናል ያበረታታናል፡፡ እሳቱን የሚቆሰቁሰው የእግዚአብሄር ቃል ከሌለን እግዚአብሄር በህይወታችን ያየውን ለመውረስ እንዘረጋም፡፡ እግዚአብሄ ለእኛ ያለውን ለማግኘት ካልተዘረጋን ደግሞ አንወርስም፡፡
እንግዲህ ታላቅ ብድራት ያለውን ድፍረታችሁን አትጣሉ። የእግዚአብሔርን ፈቃድ አድርጋችሁ የተሰጣችሁን የተስፋ ቃል እንድታገኙ መጽናት ያስፈልጋችኋልና። ዕብራውያን 10፡25-36
የእግዚአብሄር ቃል ማበረታቻና እሳታቸውን ጠብቀው እግዚአብሄርን ደስ ያሰኙ የቅዱሳን ህይወት ምስክርነት ልባችንን ያቀጣጥለዋል፡፡ 
እንግዲህ እነዚህን የሚያህሉ ምስክሮች እንደ ደመና በዙሪያችን ካሉልን፥ እኛ ደግሞ ሸክምን ሁሉ ቶሎም የሚከበንን ኃጢአት አስወግደን፥ የእምነታችንንም ራስና ፈጻሚውን ኢየሱስን ተመልክተን፥ በፊታችን ያለውን ሩጫ በትዕግሥት እንሩጥ፤ እርሱ ነውርን ንቆ በፊቱም ስላለው ደስታ በመስቀል ታግሦ በእግዚአብሔር ዙፋን ቀኝ ተቀምጦአልና። በነፍሳችሁ ዝላችሁ እንዳትደክሙ፥ ከኃጢአተኞች በደረሰበት እንዲህ ባለ መቃወም የጸናውን አስቡ። ዕብራውያን 12፡1-3
3.     ጭንቀትና የኑሮ ፍርሃት
ሰው ሲፈራ ጉልበቱ ይክደዋል፡፡ ጀግንነት ግን የፍርሃትን ስሜት የማይሰማው ሳይሆን የሚሰማውን የፍርሃት ስሜት ተቀብሎ ከአላማው የማይቆም ሰው ነው፡፡ ድፍረት የፍርሃትን ስሜት አለመስማት አለመቀበል ነው፡፡ የፍርሃት ስሜት ይመጣል ነገር ግን እየፈራንም ቢሆን የእግዚአብሄርን ፈቃድ ካደረግን ፍርሃት እኛን የማስቆም አላማውን መፈፀም ያቅተዋል፡፡
በእሾህም የተዘሩት ሌሎች ናቸው፥ ቃሉን የሰሙት እነዚህ ናቸው፥ የዚህም ዓለም አሳብና የባለጠግነት ማታለል የሌላውም ነገር ምኞት ገብተው ቃሉን ያንቃሉ፥ የማያፈራም ይሆናል። ማርቆስ 4፡18-19
4.     የቅዱሳን ህብረት እጥረት
እርስ በእርሳችን የምንቀጣጠልበት ማቀጣጠያ እሳት በእያንንዳችን ውስጥ አለ፡፡ ስንሰበሰብ የእግዚአብሄርን ነገር ስናወጋ ስንበረታታ እሳታችን ይለኮሳል፡፡ የወንድሞች የፀጋ ቃል ባለንበት እንዳንቆም ከከበበን ነገሮች አልፈን እንድንዘረጋ አቅማችንን ያድሳል፡፡
ለፍቅርና ለመልካምም ሥራ እንድንነቃቃ እርስ በርሳችን እንተያይ፤ በአንዳንዶችም ዘንድ ልማድ እንደ ሆነው፥ መሰብሰባችንን አንተው እርስ በርሳችን እንመካከር እንጂ፤ ይልቁንም ቀኑ ሲቀርብ እያያችሁ አብልጣችሁ ይህን አድርጉ። ዕብራውያን 10፡24-25
ለተጨማሪ ፅሁፎች https://www.facebook.com/abiy.wakuma/notes
ለቪዲዮ መልእክቶች https://www.youtube.com/user/awordm/videos

#ኢየሱስ #ጌታ #እሳት #ህብረት #ቃል #መቀጣጠል #ክብር #አገልግሎት #መዋረድ #መርካት #ፀጋ #እውቀት #ኢየሱስንተመልክተን #አማርኛ #ስብከት #መዳን #መፅሃፍቅዱስ #ብፅእና #እምነት #ታላቅነት #ማገልገል #አቢይ #አቢይዋቁማ #አቢይዋቁማዲንሳ

No comments:

Post a Comment