Popular Posts

Thursday, September 7, 2017

ባልንጀራዬስ ማን ነው?

እነሆም፥ አንድ ሕግ አዋቂ ሊፈትነው ተነሥቶ፦ መምህር ሆይ፥ የዘላለምን ሕይወት እንድወርስ ምን ላድርግ? አለው። እርሱም በሕግ የተጻፈው ምንድር ነው? እንዴትስ ታነባለህ? አለው። እርሱም መልሶ፦ ጌታ አምላክህን በፍጹም ልብህ በፍጹም ነፍስህም በፍጹም ኃይልህም በፍጹም አሳብህም ውደድ፥ ባልንጀራህንም እንደ ራስህ ውደድ አለው። ኢየሱስም፦ እውነት መለስህ፤ ይህን አድርግ በሕይወትም ትኖራለህ አለው። እርሱ ግን ራሱን ሊያጸድቅ ወድዶ ኢየሱስን፦ ባልንጀራዬስ ማን ነው? አለው። ኢየሱስም መልሶ እንዲህ አለ፦ አንድ ሰው ከኢየሩሳሌም ወደ ኢያሪኮ ወረደ በወንበዴዎችም እጅ ወደቀ፤ እነርሱም ደግሞ ገፈፉት ደበደቡትም በሕይወትና በሞት መካከልም ትተውት ሄዱ። ድንገትም አንድ ካህን በዚያ መንገድ ወረደ አይቶትም ገለል ብሎ አለፈ። እንዲሁም ደግሞ አንድ ሌዋዊ ወደዚያ ስፍራ መጣና አይቶት ገለል ብሎ አለፈ። አንድ ሳምራዊ ግን ሲሄድ ወደ እርሱ መጣ አይቶትም አዘነለት፥ ቀርቦም ዘይትና የወይን ጠጅ በቍስሎቹ ላይ አፍስሶ አሰራቸው፥ በራሱ አህያም ላይ አስቀምጦት ወደ እንግዶች ማደርያ ወሰደው  ጠበቀውም። በማግሥቱም ሁለት ዲናር አውጥቶ ለባለቤቱ ሰጠና፦ ጠብቀው፥ ከዚህም በላይ የምትከስረውን ሁሉ እኔ ስመለስ እከፍልሃለሁ አለው። እንግዲህ ከነዚህ ከሦስቱ በወንበዴዎች እጅ ለወደቀው ባልንጀራ የሆነው ማንኛው ይመስልሃል? እርሱም፦ ምሕረት ያደረገለት አለ። ኢየሱስም፦ ሂድ አንተም እንዲሁ አድርግ አለው። ሉቃስ 1025-37
የህግ መምህር ኢየሱስ ላነሳው የባልንጀራህን እንደራስህ ውደድ ትእዛዝ የማይፈፅምበት ሰበብ አገኘለት፡፡ የህግ መምህሩ የኢየሱስን ባልንጀራህን እንደራስህ አድርገህ ውደድ ትእዛዝን የማይፈጽምበት በቂ ምክኒያት ያለው መሰለው፡፡ የህግ መምህሩ ባልንጀራ የለኝም ስለዚህ ይህንን ባልንጀራህን እንደራስህ አድርገህ ውደድ የሚለውን ትእዛዝ እንዴት ልፈፅም እችላለሁ የሚል ጥያቄ አነሳ፡፡
በህግ መምህሩ አይን ባልንጀራ ማለት አንድ ነገር ስታደርጉለት መልሶ አንድ ነገር የሚያድርግላችሁ አኩያ ማለት ነው፡፡ ባልንጀራ ማለት መልካም ስታደርጉለት መልካም የሚያደርግ ሰው ነው፡፡ ለህግ መምህሩ ባልንጀርነት በእናንተ መንፈሳዊ ደረጃ የሚኖር ማለት ነው፡፡ ለህግ መምህሩ ባለንጀራ ማለት እንደ እርሱ መንፈሳዊ የሆነ ንፁህ ሰው ማለት ነው፡፡ ለህግ መምህሩ ባልንጀርነት የእንካ በእንካ ፍቅር ነው፡፡
ለህግ መምህሩ ባልንጀራዬ የሚለው ሲጋበዝ መልሶ የሚጋብዝ ፣ ስጦታ ሲሰጠው መልሶ የሚሰጥ ፣ መልካም ሲያደርጉለት መልሶ የሚያደርገውን ሰው ነው፡፡ ለህግ መምህሩ ባልንጀራ ማለት በመንፈሳዊ ደረጃ የሚመጣጠን ህጉን እንዳንተ የሚጠብቅ ቅዱስ ሰው ማለት ነው፡፡
በህግ መምህሩ አይን ባልንጀራ የሚፈራው እኩያን ፈልጎ በማግኘትና እኩል ለእኩል በመረዳዳት ነው፡፡  
በኢየሱስ አይን ደግሞ ባልንጀራ የሚፈራው ለሰው መልካም በማድረግ ነው፡፡
መልካም ለምረታደርግላቸው ሰዎች ሁሉ ባልንጀራቸው ነህ፡፡ ባልንጀራ ከፈለክ መልካም አድርግ፡፡ ባልንጀራ ለመባል መልካም የምታደርግለት ሰው ማግኘት ይበቃል፡፡ ባልንጀራ ለማፍራት መልካም ስታደርግለት መልካም የሚያደርግልህ ሰው መጠበቅ የለብህም፡፡ ባልንጀራ ከፈለግክ መልካም አድርግ፡፡ መልካም ለምታደርግለት ሰው ባልንጀራው ነህ፡፡ መልካም የምታደርግለት ሰው ሁሉ ሃብትህ ነው፡፡ መልካም የምታድርግለት ሰው ሁሉ ጌጥህ ነው፡፡ መልካም የምታደርግለት ሰው ሁሉ ክብርህ ነው፡፡  
ወዳጅ ማብዛት ትፈልጋለህ መልካም ማድረግህን አብዛ፡፡ መልካም ላደረክላቸው ሰዎች ሁሉ ባልንጀራቸው ነህ፡፡ መልካም ላደረክላቸው ሰዎች ሁሉ ውድ ሰው ነህ፡፡ መልካም ላደረክላቸው ሰዎች ሁሉ ፊት ዝነኛ ነህ፡፡ መልካም ላደረግክላቸው ሰዎች ሁሉ ባለጠጋ ነህ፡፡ መልካም ላደረግክላቸው ሰዎች ከአንተ በላይ ባለመድሃኒት የለም፡፡
እንግዲህ ከነዚህ ከሦስቱ በወንበዴዎች እጅ ለወደቀው ባልንጀራ የሆነው ማንኛው ይመስልሃል? እርሱም፦ ምሕረት ያደረገለት አለ። ኢየሱስም፦ ሂድ አንተም እንዲሁ አድርግ አለው። ሉቃስ 10፡37
ለተጨማሪ ፅሁፎች https://www.facebook.com/abiy.wakuma/notes
ለቪዲዮ መልእክቶች https://www.youtube.com/user/awordm/videos

#ኢየሱስ #ጌታ #እምነት #ፍቅር #መውደድ #ማድረግ #መስጠት #አማርኛ #ስብከት #መዳን #መፅሃፍቅዱስ #ልብ #ቸርነት #ሳምራዊ #ሌዋዊ #ካህን #ባልጀራህን #አቢይ #አቢይዋቁማ #አቢይዋቁማዲንሳ #እወጃ #ወንጌል #ፅናት #ትግስት #መሪ

No comments:

Post a Comment