Popular Posts

Saturday, September 2, 2017

ባል ሚስቱን እንዲወዳት የምታበረታታበት መንገድ

ሚስቶች ሆይ፥ ለጌታ እንደምትገዙ ለባሎቻችሁ ተገዙ፤ ክርስቶስ ደግሞ የቤተ ክርስቲያን ራስ እንደ ሆነ እርሱም አካሉን የሚያድን እንደ ሆነ ባል የሚስት ራስ ነውና። ዳሩ ግን ቤተ ክርስቲያን ለክርስቶስ እንደምትገዛ እንዲሁ ሚስቶች ደግሞ በሁሉ ለባሎቻቸው ይገዙ።  ኤፌሶን 5፡22-25
ሰውን አንዳንዴ መውደድ  ይቀላል፡፡ ሰውን ሁልጊዜ መውደድ ግን ቀላል አይደለም፡፡ ሰውን በብርታቱ መውደድ ይቀላል፡፡ ሰውን በድካሙ መውደድ ግን እንደዚያ ቀላል አይደለም፡፡ ሰውን መውደድ መውደድ ሲያሰኘን መውደድ ቀላል ነው፡፡ ሰውን መውደድ ሳይሰማን መውደድ ግን ቀላል አይደለም፡፡  
አንዳንድ ሴቶች የወንድ የመውደድ ሃላፊነት ከሴት የመገዛት ሃላፊነት ይቀላል ይላሉ፡፡ እውነት ነው ሰው መውደድ መውደድ ሲሰማው መውደድ ይቀለዋል፡፡ ነገር ግን ባል መውደድ ሲሰማው ሳይሆን የወደው ባል ሚስቱን የሚወዳት ከየትኛውም ምክኒያት ጋር ተያይዞ አይደለም፡፡ መፅሃፍ ቅዱስ ክርስቶስ እኛን ጠላቶች ሳለን ካለምክኒያት እንደወደደን ባል ሚስቱን ካለምክኒያት እንዲወዳት ያዛል፡፡ ክርስቶስ ካለምክኒያት እንደማይወደን ፍቅሩ በሁኔታዎች እንደማይለወጥና እኛን ለመውደድ ራሱን እንደሰጠ ባል ሚስቱን እንዲወድ የመፅሃፍ ቅዱስ ትእዛዝ ነው፡፡  
ክርስቶስ ደግሞ ቤተ ክርስቲያንን እንደ ወደዳት ሚስቶቻችሁን ውደዱ፡፡ ኤፌሶን 5፡25-26
የወንድ የመውደድ ሃላፊነት የሚቀልበት ጊዜ አለው፡፡ ነገር ግን ባል ሚስቱን መውደድ ያለበት ሚስቱ ስትደክምና የራስዋን ሃላፊነትም ሳትወጣ ነው፡፡ ባል ሚስቱ ባለችበት በምንም ሁኔታ ውስጥ ሊወዳትና ከምንም ምክኒያት ጋር ባለተያያዘ መልኩ የባልነት የመውደድ ሃላፊነቱን ሊወጣ ይገባዋል፡፡
ፍቅር የውሳኔ ጉዳይ ነው፡፡ ፍቅር የስሜት ጉዳይ አይደለም፡፡ ፍቅር የመረዳት እርምጃ ነው፡፡ ባል ሚስቱን መውደድ ራስን የመስጠት ጉዳይ ነው፡፡
ነገር ግን ይህን ካለ ምክኒያይት የመውደድ ሃላፊነቱን እንዲወጣ ሚስት የምታደረገው ማበረታቻ አለ፡፡ ሚስት ባሌ እንዴት ሊወደኝ ይገባል በማለት በባል ሃላፊነት በጭንቀት ጊዜ ከምታጠፋ እንዴት ልታዘዝለት ብላ ብታስብ ባልዋ ሁልጊዜ እንዲወዳት በተዘዋዋሪ መንገድ ማበረታታት ትችላለች፡፡ ባል በምንም ሁኔታ ውስጥ ሚስቱን መውደድ ይገባዋል፡፡ ሚስት ግን በመታዘዝና ባለመታዘዝ ባልዋ እንዲወዳት ማበረታታትም አለማበረታታትም ትችላለች፡፡ ወይም እርስዋን መውደዱን ደስ ብሎት እንዳያደርገው ልታከብድበት ትችላለች፡፡    
ለዋኖቻችሁ ታዘዙና ተገዙ፤ እነርሱ ስሌትን እንደሚሰጡ አድርገው፥ ይህንኑ በደስታ እንጂ በኃዘን እንዳያደርጉት፥ ይህ የማይጠቅማችሁ ነበርና፥ ስለ ነፍሳችሁ ይተጋሉ። ዕብራዊያን 13፡17
ሚስት ትዳሬ ከእኔ ምን ይፈልጋል በሚለው ሃላፊነት ለባልዋ በመታተዝ ላይ ካተኮረች ባልዋ እርስዋን ሁልጊዜ እንዲወዳት ጉልበት ትጨምርለታለች፡፡ ሚስት ግን ባል ሚስቱን ይወደዳት ውደደኝ ብላ ብትጨቃጨቅ እንደ ብሉይ ኪዳን ህግ ባልዋ የሚያውቅውን ነገር ትነግረዋለች እንጂ የባልነት የመውደድ ሃላፊነቱን እንዲፈፅም አትረዳውም፡፡ ወይም ባሌ እንደሚገባው አይወደኝም ብለሽ ብታሚ ባልሽ ይበልጥ እንዲወድሽ ለእርሱ ይበልጥ በመታዘዝ ያደረግሽው አስተዋፅኦ ስለሌለ ከባልሽ አልፈሽ ህጉን ታሚያለሽ እንጂ ባልሽ ህጉን እንዲፈፅም ያደረግሽው አስተዋፅኦ የለም፡፡
በጌታ ፊት ራሳችሁን አዋርዱ ከፍ ከፍም ያደርጋችኋል። ወንድሞች ሆይ፥ እርስ በርሳችሁ አትተማሙ። ወንድሙን የሚያማ በወንድሙም የሚፈርድ ሕግን ያማል በሕግም ይፈርዳል፤ በሕግም ብትፈርድ ፈራጅ ነህ እንጂ ሕግን አድራጊ አይደለህም። ያዕቆብ 4፡10-11
ሚስት ሁሌ መጠየቅ ያለባት እኔ ለትዳሬ ምን አድርጌያለሁ? ትዳሬ ከእኔ ምን ይፈልጋል? የሚለውን ጥያቄ እንጂ የራስዋን የመታዘዝ ሃላፊነት ትታ ባሌ ስለሃላፊነቱ ምን እያደረገ ነው? በሚለው ጥያቄ ላይ ካተኮረችና ባተሌ ከሆነች የሚለወጥ ነገር አይኖረም፡፡
ሚስት ለባልዋ በሁሉ በታዘዘች መጠን ባልዋ በሁሉ እንዲወዳት ካለ ንግግር እና ካለቃል ታበረታታዋለች፡፡
እንዲሁም፥ እናንተ ሚስቶች ሆይ፥ ከባሎቻችሁ አንዳንዱ ለትምህርት የማይታዘዙ ቢኖሩ፥ በፍርሃት ያለውን ንጹሑን ኑሮአችሁን እየተመለከቱ ያለ ትምህርት በሚስቶቻቸው ኑሮ እንዲገኙ ተገዙላቸው። 1ኛ ጴጥሮስ 3፡1-2
ለተጨማሪ ፅሁፎች https://www.facebook.com/abiy.wakuma/notes
ለቪዲዮ መልእክቶች https://www.youtube.com/user/awordm/videos

#ኢየሱስ #ጌታ #ህይወት #ጋብቻ #ትዳር #ባል #ሚስት #ፍቅር #መውደድ #መታዘዝ #ይተዋል #ይጣበቃል #አንድስጋ #እውነት #ትህትና #ትንሳኤ #ህይወት #ወንጌል #አማርኛ #ስብከት #መዳን #መፅሃፍቅዱስ #መንፈስቅዱስ  #ፌስቡክ #አቢይዋቁማ #አቢይዋቁማዲንሳ  

No comments:

Post a Comment