Popular Posts

Sunday, September 3, 2017

ምድር ሁሉ ከክብሩ ተሞልታለች

ቅዱስ ቅዱስ ቅዱስ እግዚአብሔር፤ ምድር ሁሉ ከክብሩ ተሞልታለች ኢሳያስ 63      
የእግዚአብሄርን አሰራር በተረዳን መጠን እናርፋለን፡፡ የእግዚአብሄርን አሰራር በተረዳን መጠን በስራው መተባበር እንችላለን፡፡ የእግዚአብሄርን አሰራር በተረዳን መጠን በምንሰራው ሁሉ ፍሬያማ እንሆናለን፡፡
እግዚአብሄር የምድር ፈጣሪና ባለቤት ነው፡፡ እግዚአብሄር ምድርንና ሰውን የፈጠረው ለክብሩ ነው፡፡ እግዚአብሄር ምድርን አያስተዳደረ ነው፡፡
እግዚአብሄር አንዳንዴ ከምናስበው በላይ በትጋት እየሰራ ነው፡፡ እግዚአብሄር ስለጥቃቅኑም ነገር ግድ ይለዋል፡፡
ሁለት ድንቢጦች በአምስት ሳንቲም ይሸጡ የለምን? ከእነርሱም አንዲቱ ያለ አባታችሁ ፈቃድ በምድር ላይ አትወድቅም። የእናንተስ የራሳችሁ ጠጉር ሁሉ እንኳ ተቈጥሮአል። ማቴዎስ 10፡29-30
እግዚአብሄር ሰዎችን ፍቃድ ያላቸው አድርጎ ቢፈጥራቸውም እግዚአብሄር ምድርግን በፈለገው መንገድ ምድርን እያስኬደ ነው፡፡ እግዚአብሄርን ንጉስ ነው፡፡
እግዚአብሔር ለምድር ሁሉ ንጉሥ ነውና፤ በማስተዋል ዘምሩ። እግዚአብሔር በአሕዛብ ላይ ነገሠ፤ እግዚአብሔር በቅድስናው ዙፋን ይቀመጣል። መዝሙር 47፡7-8
እግዚአብሄር የአላማ አምላክ ነው፡፡ እግዚአብሄር ምን መስራት እንደሚፈልግ ያውቃል፡፡ እግዚአብሄር በእያንዳንዱ ነገር ላይ አላማ አለው፡፡ እግዚአብሄር አላማውን ለማሳካት በትጋር እየሰራ ነው፡፡ እግዚአብሄር በስራ ላይ ነው፡፡
ኢየሱስ ግን፦ አባቴ እስከ ዛሬ ይሠራል እኔም ደግሞ እሠራለሁ ብሎ መለሰላቸው። ዮሃንስ 5፡17
ለእግዚአብሄር ሃሳብ አንሰጠውም፡፡ እግዚአብሄር በምድር ላይ ምን ማድረግ እንደሚፈልግ ያውቃል፡፡
ለእናንተ የማስባትን አሳብ እኔ አውቃለሁ፤ ፍጻሜና ተስፋ እሰጣችሁ ዘንድ የሰላም አሳብ ነው እንጂ የክፉ ነገር አይደለም። ኤርሚያስ 29፡11
የተሻለ ነገር ብናደርግ ቀድሞውኑ በስራ ላይ ካለው ከእግዚአብሄር ጋር መተባበር ነው፡፡ የሚሳካልን ምድር ሁሉ ከክብሩ እንደተሞላች አስተውለን ከእገዚአብሄር ጋረ አብረን ስንሰራ ነው፡፡ ከእግዚአብሄር ጋር አብረን ሰራተኛ ነን፡፡ ምክኒያቱም ምድር ሁሉ ከክብሩ ተሞልታለችና፡፡
የእግዚአብሔር እርሻ ናችሁ፤ የእግዚአብሔር ሕንፃ ናችሁ፤ ከእርሱ ጋር አብረን የምንሠራ ነንና። 1ኛ ወደ ቆሮንቶስ ሰዎች 3፡9
የእግዚአብሄር መንግስት በሃይል እየሰራች ነው፡፡ የእግዚአብሄር መንግስት እየሰራች መሆኑን በአይናችን አላየንም ማለይት ስራዋን አቁማለች ማለት አይደለም፡፡ የእግዚአብሄር መንግስት በምድር ላይ በሃይልና በትጋት እየሰራች ነው፡፡
ፈሪሳውያንም፦ የእግዚአብሔር መንግሥት መቼ ትመጣለች ብለው ቢጠይቁት፥ መልሶ፦ የእግዚአብሔር መንግሥት በመጠባበቅ አትመጣም፤ ደግሞም፦ እንኋት በዚህ ወይም፦ እንኋት በዚያ አይሉአትም። እነሆ፥ የእግዚአብሔር መንግሥት በመካከላችሁ ናትና አላቸው። ሉቃስ 17፡20-21
የእግዚአብሄር አሰራር እንደ እርሾ ነው፡፡ እግዚአብሄር ፈጥኖ ሲሰራ አይታይም ግን እየለወጠ ነው፡፡ የእግዚአብሄርን አላማ ሊያደናቅፍና በፊቱ ሊቆም የሚችል ምንም ሃይል የለም፡፡
ሌላ ምሳሌ ነገራቸው እንዲህም አለ፦ መንግሥተ ሰማያት ሁሉ እስኪቦካ ድረስ ሴት ወስዳ በሦስት መስፈሪያ ዱቄት የሸሸገችውን እርሾ ትመስላለች። ማቴዎስ 13፡33
በፍጥረት ወቅት የእግዚአብሄር መንፈስ በጥልቁ ላይ እንደነበረ ሁሉ ምድር በእግዚአብሄር ክብር ተሞልታለች፡፡ /ዘፍጥረት 1፡3/ ከእግዚአብሄር እውቀትና ሃይል የሚያመልጥ ምንም ነገር የለም፡፡
ስንፀልይ እንኳን ምድር ሁሉ ከክብሩ እንደተሞላችና ከእግዚአብሄር ክብር የሚያመልጥ ነገር እንደሌለ በማመን በእረፍት ነው፡፡
መንግሥት ያንተ ናትና ኃይልም ክብርም ለዘለዓለሙ፤ አሜን። ማቴዎስ 6፡13
ምድር ሁሉ ከክብሩ ተሞልታለች፡፡ ኢሳያስ 6፡3
ለተጨማሪ ፅሁፎች https://www.facebook.com/abiy.wakuma/notes
ለቪዲዮ መልእክቶች https://www.youtube.com/user/awordm/videos

#ኢየሱስ #ጌታ #ክብር #ሃይል #ዘላለም #ጥበብ #የእግዚአብሄርመንግስት #ንጉስ #እርሾ #አማርኛ #ስብከት #መዳን #መፅሃፍቅዱስ #ብፅእና  #አቢይ #አቢይዋቁማ #አቢይዋቁማዲንሳ

No comments:

Post a Comment