Popular Posts

Thursday, September 21, 2017

በእውቀት ጸጋና ሰላም ይብዛላችሁ

የመለኮቱ ኃይል፥ በገዛ ክብሩና በበጎነቱ የጠራንን በማወቅ፥ ለሕይወትና እግዚአብሔርን ለመምሰል የሚሆነውን ነገር ሁሉ ስለ ሰጠን፥ በእግዚአብሔርና በጌታችን በኢየሱስ እውቀት ጸጋና ሰላም ይብዛላችሁ። 2ኛ ጴጥሮስ 1፡2-3
በመጀመሪያም ሰው የተፈጠረው በእግዚአብሄር መልክና አምሳል ነው፡፡ የሰው የእግዚአብሄር መልክ እና አምሳል የጠፋው ሰው በሃጢያት ሲወድቅ ነው፡፡ በኢየሱስ የሃጢያታችን እዳ የተከፈለው ወደዚህ ወደጥንቱ የመለኮት ህብረት እንድንመለስ ነው፡፡ እግዚአብሄር በመለኮት ክብር ጠርቶናል፡፡ እግዚአብሄር በዚህ በታላቅ ክብር ቢጠራንም እውቀቱ ከሌላን እንደ ተራ ሰው ልንኖር እንችላለን፡፡ እግዚአብሄር በመለኮት ሃይል ቢጠራንም እንደ ደካማ ተሸናፊ ልንሆን እንችላለን፡፡ ስለዚህ ነው እውቀት ወሳኝ የሆነው፡፡
እውቀታችን ባደገ ቁጥር ፀጋ ይበዛልናል፡፡
ህይወትን በሚገባ ለመያዝ ሃይል ይጠይቃል፡፡ አንድ ነገርን ለእግዚአብሄር ለማድረግ የእግዚአብሄር የሚያስችል ሃይል ወሳኝ ነው፡፡ ኢየሱስን ለተቀበለ ሰው ሁሉ የሚያስችል ሃይል የእግዚአብሄር ፀጋ ተዘጋጅቶዋል፡፡ በዚህ ፀጋ ለመኖር በዚህ የሚያስችል ሃይል ተጠቃሚ ለመሆንና ለእግዚአብሄር ለመኖርና እግዚአብሄርን ለማገልገል እውቀት ያስፈልገናል፡፡ እውቀታችን ሲበዛ በህይወታችን የሚሰራው ፀጋ ይበዛል፡፡ እውቀታችን ሲበዛ ለህይወትና እግዚአብሄርን ለመምሰል የተሰጠንን ተረድተን በዚያ መብት መመላለስ እንጀምራለን፡፡ እውቀታችን በበዛ መጠን በህይወታችን የሚፈሰው ፀጋ ይበዛል፡፡ እውቀታችን በበዛ መጠን በህይወታችን ያለውን የእግዚአብሄርን አላማ ፈፅመን ማለፍ እንችላለን፡፡
እውቀታችን ባደገ ቁጠር ሰላማችን ይበዛልናል፡፡
አሁን ያለን የሰላም መጠን ያለንን የእውቀት መጠን ያሳያል፡፡ እግዚአብሄር ለህይወትና እግዚአብሄርን ለመምሰል የሚያስፈልገንን ሁሉ ቢሰጠንም ካለን እውቀት መጠን በላይ ሰላም ሊኖረን አይችልም፡፡ እውቀታችን ሲጨምር ሰላማችን ይጨምራል፡፡ እውቀታችን ሲበዛ ሰላማችን ይበዛል፡፡
የመለኮቱ ኃይል፥ በገዛ ክብሩና በበጎነቱ የጠራንን በማወቅ፥ ለሕይወትና እግዚአብሔርን ለመምሰል የሚሆነውን ነገር ሁሉ ስለ ሰጠን፥ በእግዚአብሔርና በጌታችን በኢየሱስ እውቀት ጸጋና ሰላም ይብዛላችሁ። 2 ጴጥሮስ 12-3
ለተጨማሪ ፅሁፎች https://www.facebook.com/abiy.wakuma/notes
ለቪዲዮ መልእክቶች https://www.youtube.com/user/awordm/videos
#እውቀት #ጥበብ #ነፍስ #መዳን #ኢየሱስ #ጌታ #እግዚአብሔር #ፀጋ #መልካም #መታዘዝ #መሪነት #ቤተክርስትያን #አማርኛ #ስብከት #መዳን #መፅሃፍቅዱስ #መጋቢ #እምነት #ተስፋ #ፍቅር #ጌታ #ሰላም #ደስታ #አቢይ #አቢይዋቁማ #አቢይዋቁማዲንሳ #እወጃ #መናገር #አእምሮ #ሰላም #ማስተዋል #ልጅ

No comments:

Post a Comment