Popular Posts

Monday, August 28, 2017

ትዳር የእግዚአብሔር ስርአት

ትዳር የሰው ሃሳብ አይደለም፡፡ ትዳር የሰው ፈጠራ አይደለም፡፡ ትዳር የሰው እቅድ አይደለም፡፡ ትዳር የእግዚአብሔር ሃሳብ ነው፡፡ ትዳር እግዚአብሔር ራሱ ያቋቋመው ተቋም ነው፡፡ ትዳር የእግዚአብሔር ስርአት ነው፡፡
እግዚአብሔር አምላክም አለ፦ ሰው ብቻውን ይሆን ዘንድ መልካም አይደለም፤ የሚመቸውን ረዳት እንፍጠርለት። ዘፍጥረት 2፡18
አዳምም ለእንስሳት ሁሉ፥ ለሰማይ ወፎችም ሁሉ፥ ለምድር አራዊትም ሁሉ ስም አወጣላቸው፤ ነገር ግን ለአዳም እንደ እርሱ ያለ ረዳት አልተገኘለትም ነበር። እግዚአብሔር አምላክም በአዳም ከባድ እንቅልፍን ጣለበት፥ አንቀላፋም፤ ከጎኑም አንዲት አጥንትን ወስዶ ስፍራውን በሥጋ ዘጋው። እግዚአብሔር አምላክም ከአዳም የወሰዳትን አጥንት ሴት አድርጎ ሠራት፤ ወደ አዳምም አመጣት። አዳምም አለ፦ ይህች አጥንት ከአጥንቴ ናት፥ ሥጋም ከሥጋዬ ናት፤ እርስዋ ከወንድ ተገኝታለችና ሴት ትባል። ስለዚህ ሰው አባቱንና እናቱን ይተዋል፥ በሚስቱም ይጣበቃል፤ ሁለቱም አንድ ሥጋ ይሆናሉ። አዳምና ሚስቱ ሁለቱም ዕራቁታቸውን ነበሩ፥ አይተፋፈሩም ነበር። ዘፍጥረት 2፡20-25
ትዳርን አለመቃወም የእግዚአብሄርን መንግስት አለመቃወም ነው፡፡ ትዳርን አለመቃወም የእግዚአብሄርን አሰራር አለመቃወም ነው፡፡ ለትዳር መስራት ለእግዚአብሄር መንግስት መስራት ነው፡፡ ትዳርን ማክበር የእግዚአብሄርን ስርአት ማክበር ነው፡፡ ትዳርን መውደድ እግዚአብሔርን መውደድ ነው፡፡ ትዳርን ማክበር እግዚአብርን ማክበር ነው፡፡
መጋባት በሁሉ ዘንድ ክቡር መኝታውም ንጹሕ ይሁን፤ ሴሰኞችንና አመንዝሮችን ግን እግዚአብሔር ይፈርድባቸዋል። ዕብራውያን 13፡4
ትዳርን መቃወም የእግዚአብሔርን ስርአት መቃወም ነው፡፡ ትዳርን መቃወም አግዚአብሔርን መቃወም ነው፡፡ የትዳር መጠንከር የእግዚአብሔር መንግስት መጠንከር አንዱ አካል ነው፡፡
ስለዚህ ባለ ሥልጣንን የሚቃወም የእግዚአብሔርን ሥርዓት ይቃወማል፤ የሚቃወሙትም በራሳቸው ላይ ፍርድን ይቀበላሉ። ሮሜ 13፡2
ኢየሱስ ስለመጋባት ሲናገር በመጀመሪያ ግን እንደዚህ አልነበረም በማለት የእግዚአብሄርን ሃሳብ ለመረዳት የመጀመሪያውን የጥንቱን የእግዚአብሄርን ሃሳብ መረዳት ወሳኝ እንደሆነ ይነግረናል፡፡
እርሱ ግን መልሶ እንዲህ አለ፦ ፈጣሪ በመጀመሪያ ወንድና ሴት አደረጋቸው፥ አለም፦ ስለዚህ ሰው አባቱንና እናቱን ይተዋል፥ ከሚስቱም ጋር ይተባበራል፥ ሁለቱም አንድ ሥጋ ይሆናሉ የሚለውን ቃል አላነበባችሁምን? ስለዚህ አንድ ሥጋ ናቸው እንጂ ወደ ፊት ሁለት አይደሉም። እግዚአብሔር ያጣመረውን እንግዲህ ሰው አይለየው። እነርሱም፦ እንኪያስ ሙሴ የፍችዋን ጽሕፈት ሰጥተው እንዲፈቱአት ስለ ምን አዘዘ? አሉት። እርሱም፦ ሙሴስ ስለ ልባችሁ ጥንካሬ ሚስቶቻችሁን ትፈቱ ዘንድ ፈቀደላችሁ፤ ከጥንት ግን እንዲህ አልነበረም። ማቴዎስ 19፡4-8
የመጀመሪያው ኦሪጂናል የእግዚአብሄር ሃሳብ እውነት ነው፡፡ ሰው የሚጠቀመው ከእውነት ጋር ሲስማማ ነው እንጂ ከእውነት ተቃራኒ ሲሆን አይደለም፡፡ ሰው ከእውነት ተቃራኒ ሲሆን ይጎዳል፡፡ እጅግ ጠቢብ ሰው ከእውነት ጋር ይወግናል እንጂ በእውነት ላይ ምንም ሊያደርግ አይችልም፡፡  
ሐዋሪያው ጳውሎስ ከእውነት ጋር መወገን እንጂ ከኦሪጂናል በእግዚአብሄር ሃሳብ ላይ ወይም በእውነት ላይ ምንም ማድረግ እንደማይችል የተናገረው፡፡
ለእውነት እንጂ በእውነት ላይ ምንም ለማድረግ አንችልምና። 2ኛ ቆሮንቶስ 13፡8
ስለዚህ ነው ኢየሱስ እግዚአብሔር ያጣመረውን እንግዲህ ሰው አይለየው በማለት የሚያስጠነቅቀን፡፡
እግዚአብሔር ያጣመረውን እንግዲህ ሰው አይለየው። ማርቆስ 10፡9
ሁላችሁም እርስ በርሳችሁ እየተዋረዳችሁ ትሕትናን እንደ ልብስ ታጠቁ፥ እግዚአብሔር ትዕቢተኞችን ይቃወማልና፥ ለትሑታን ግን ጸጋን ይሰጣል። እንግዲህ በጊዜው ከፍ እንዲያደርጋችሁ ከኃይለኛው ከእግዚአብሔር እጅ በታች ራሳችሁን አዋርዱ፤ 1ኛ ጴጥሮስ 5፡5-6
ለተጨማሪ ፅሁፎች https://www.facebook.com/abiy.wakuma/notes
ለቪዲዮ መልእክቶች https://www.youtube.com/user/awordm/videos

#ኢየሱስ #ጌታ #ህይወት #ጋብቻ #ትዳር #ባል #ሚስት #አንድስጋ #እውነት #ትህትና #ትንሳኤ #ህይወት #ወንጌል #አማርኛ #ስብከት #መዳን #መፅሃፍቅዱስ #መንፈስቅዱስ  #ፌስቡክ #አቢይዋቁማ #አቢይዋቁማዲንሳ  

No comments:

Post a Comment