Popular Posts

Wednesday, June 21, 2017

ገንዘብን ከሚቀበል ይልቅ የሚሰጥ ይበልጥ የተባረከበት ዋና ዋና ምክኒያቶች

ገንዘብን መስጠት ጥልቅ የሆነ መነሻ ሃሳብ አለው፡፡ ገንዘብን መስጠት ምክኒያት አለው፡፡ ገንዘቡን የሚሰጥ ሰው ገንዘቡን ለመስጠት በቂ ምክኒያት አለው፡፡ ገንዘብን መስጠት ከጀርባው ጥልቅ ምክኒያቶች አሉት፡፡
መስጠት ጥልቅ የሆነ ትርጉም አለው፡፡ ሰው ገንዘቡን ሲሰጥ በተዘዋዋሪ የሚናገረው ነገር አለው፡፡ ገንዘብን የመስጠት ትርጉምን እንመልከት፡፡
ገንዘብን መስጠት አምልኮ ነው፡፡
ገንዘብን መስጠት እግዚአብሄርን ማምለክ ነው፡፡ እግዚአብሄርን የሚያመልከ ሰው ገንዘብን አያመልክም፡፡ እግዚአብሄርን የሚወድ ሰው ገንዘብን ይጠላል እግዚአብሄርን የሚጠጋ ሰው ገንዘብን ይንቃል፡፡ ከእግዚአብሄር ጋር መልካም ግንኙነት ያለው ሰው ከገንዘብ ጋር መጥፎ ግንኙነት አይኖረውም፡፡ ለእግዚአብሄር የሚገዛ ሰው ለገንዘብ እንደማይገዛ በድርጊቱ እያወጀ ነው፡፡
ለሁለት ጌቶች መገዛት የሚቻለው ማንም የለም፤ ወይም አንዱን ይጠላል ሁለተኛውንም ይወዳል፤ ወይም ወደ አንዱ ይጠጋል ሁለተኛውንም ይንቃል፤ ለእግዚአብሔርና ለገንዘብ መገዛት አትችሉም። ማቴዎስ 6፡24
ገንዘብን መስጠት ምስጋና ነው፡፡
ገንዘብን ስንሰጥ እግዚአብሄር ነው የሰጠኝ እያልን ነው፡፡ ገንዘብን ስንሰጥ ለእግዚአብሄር አቅርቦት እውቅና እየሰጠን ነው፡፡ ገንዘብን ስንሰጥ አመሰግናለሁ እያልን ነው፡፡  
እግዚአብሔር በደስታ የሚሰጠውን ይወዳልና እያንዳንዱ በልቡ እንዳሰበ ይስጥ፥ በኀዘን ወይም በግድ አይደለም። 2ኛ ቆሮንቶስ 9፡7
ገንዘብን መስጠት እምነት ነው፡፡
ገንዘብ መተማመኛ ነው፡፡ ከገንዘብ በላይ መተማመኛ የሌለው ሰው ገንዘብን መስጠት አይችልም፡፡ ከገንዘብ በላይ የሚተማመንበት ያለው ሰው ግን ገንዘብን ይሰጣል፡፡ ገንዘብ ስጋትን ይቀንሳል፡፡ ከገንዘብ በላይ ስጋቱን የሚቀንስለትን አምላኩን የሚያውቅ ብቻ ነው ገንዘብን የሚለቀው፡፡ ገንዘብን መስጠት የማይታየውን ማየት ይጠይቃል፡፡
ብልና ዝገት በሚያጠፉት ሌቦችም ቆፍረው በሚሠርቁት ዘንድ ለእናንተ በምድር ላይ መዝገብ አትሰብስቡ፤ ነገር ግን ብልም ዝገትም በማያጠፉት ሌቦችም ቆፍረው በማይሠርቁት ዘንድ ለእናንተ በሰማይ መዝገብ ሰብስቡ፤ ማቴዎስ 6፡19-20
ገንዘብን መስጠት ፍቅር ነው፡፡
ገንዘብን የሚሰጥ ሰው ራስ ወዳድ አይደለም፡፡ ገንዘብን የሚሰጥ ሰው ሌላው ከእኔ ይሻላል ብሎ የሚያስብ ሰው ነው፡፡ ገንዘብን የሚሰጥ ሰው ሌላውን የሚያከብርና ለሌላው ዋጋ የሚሰጥ ሰው ነው፡፡ ገንዘብን የሚሰጥ ሰው ለሌላው መልካም የሚያስብ ሰው ነው፡፡  
ገንዘብን መስጠት ርህራሄ ነው፡፡
ገንዘብን መስጠት ለሌላው እንደምናስብ የምናሳይበት መንገድ ነው፡፡ ገንዘብን መስጠት ለሌላው ርህራሄ እንዳለን ያሳያል፡፡ ገንዘብን መስጠት ለራሳችን ብቻ እንዳማናስብ የምናሳይበት መንገድ ነው፡፡ ገንዘብን መስጠት በምድር ላይ ያለነው ሌላውን ለማገልገን እንደሆነ የምናሳይበት መንገድ ነው፡፡ ገንዘብን መስጠት እግዚአብሄር የሰጠን የምንበላውን ብቻ እንዳልሆነና የምንዘራውንም እንደሰጠን እውቅና የምንሰጥበት መንገድ ነው፡፡  
የሚመክርም ቢሆን በመምከሩ ይትጋ፤ የሚሰጥ በልግስና ይስጥ፤ የሚገዛ በትጋት ይግዛ፤ የሚምር በደስታ ይማር። ሮሜ 12፡8
ገንዘብን መስጠት በእግዚአብሄር መደገፍ ነው፡፡
በገንዘብ የሚደገፍ ሰው ገንዘብን አይሰጥም፡፡ ገንዘብ የህይወት ጥያቄውን ሁሉ የሚፈታለት የሚመስለው ሰው ገንዘብን አይሰጥም፡፡ ገንዘብ ግን ውስን እንደሆነ ገንዘብ ሊገዛ የማይችላቸው ብዙ ነገሮች እንዳሉና እግዚአብሄርን ከገንዘብ ውጭ ስለብዙ ነገሮች እንደምንፈልገው የተረዳ ሰው ገንዘቡን ለመስጠት አይቸግረውም፡፡ የሰው ልጅ ቁልፍ በገንዘብ ውስጥ ሳይሆን በጌታ እጅ እንዳለ ያወቀ በጌታ በመመካት ገንዘበኑን ይሰጣል፡፡  
እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፦ ጠቢብ በጥበቡ አይመካ፥ ኃያልም በኃይሉ አይመካ፥ ባለ ጠጋም በብልጥግናው አይመካ፤ ነገር ግን የሚመካው፦ ምሕረትንና ፍርድን ጽድቅንም በምድር ላይ የማደርግ እኔ እግዚአብሔር መሆኔን በማወቁና በማስተዋሉ በዚህ ይመካ፤ ደስ የሚያሰኙኝ እነዚህ ናቸውና፥ ይላል እግዚአብሔር፡፡ ኤርሚያስ 9፡23-24
ገንዘብን መስጠት መኖሪያዬ ገንዘብ አይደለም ማለት ነው፡፡
ገንዘብን መስጠት መኖሪያዬ ገንዘብ አይይደለም የሚል መልክት አለው፡፡ ገንዘብን መኖሪያቸው የሆነ ሰዎችና ከገንዘብ ኑሮ ያለፈ ነገር የማይታያቸው ሰዎች ገንዘብን አይሰጡም፡፡ ገንዘብ እንደማያኖረውና የእርሱ መኖሪያ እግዚአብሄር እንደሆነ የሚያውቀ ሰው ገንዘቡን ይሰጣል፡፡  
መኖሪያህ የዘላለም አምላክ ነው፥ የዘላለምም ክንዶች ከአንተ በታች ናቸው፤ ዘዳግም 33፡27
ሰውም ከእግዚአብሔር አፍ በሚወጣ ነገር ሁሉ በሕይወት እንዲኖር እንጂ ሰው በእንጀራ ብቻ በሕይወት እንዳይኖር ያስታውቅህ ዘንድ አስጨነቀህ፥ አስራበህም፥ አንተም ያላወቅኸውን አባቶችህም ያላወቁትን መና አበላህ። ዘዳግም 8፡3
ገንዘብን መስጠት ፀሎት ነው፡፡
ገንዘብን መስጠት እግዚአብሄርን በገንዘብ የምገዛቸውን ነገሮች አንተ አሟላ ማለት ነው፡፡ ገንዘብን መስጠት ስጡ ይሰጣችሁዋል የሚለውን እግዚአብሄርን መለመኛው መንገድ ነው፡፡ መስጠት እግዚአብሄርን ለተጨማሪ ገንዘብ መለመኛው መንገድ ነው፡፡ ገንዘቡን ሰጥቶ የሚጎድልበት ሰው ስለሌለ መስጠት በተዘዋዋሪ አይጉደልብኝ የሚል ልመና ነው፡፡
ስጡ ይሰጣችሁማል፤ በምትሰፍሩበት መስፈሪያ ተመልሶ ይሰፈርላችኋልና፥ የተጨቈነና የተነቀነቀ የተትረፈረፈም መልካም መስፈሪያ በእቅፋችሁ ይሰጣችኋል። ሉቃስ 638
ለተጨማሪ ፅሁፎች https://www.facebook.com/abiy.wakuma/notes
ለቪዲዮ መልእክቶች https://www.youtube.com/user/awordm/videos

#እምነት #መስጠት #ማካፈል #መባረክ #ስጡ #ምፅዋት #የእግዚአብሄርሃይል #መንፈስቅዱስ #መዝራት #ከልቡ #ቤተክርስትያን #አማርኛ #ስብከት #መዳን #ድሃ #መፅሃፍቅዱስ #በደስታ #ህይወት #ፌስቡክ #አቢይዋቁማ #አቢይዋቁማዲንሳ  

No comments:

Post a Comment