Popular Posts

Friday, June 9, 2017

ስለ 14ቱ የብልፅግና መገለጫዎች ሰምተዋልን ?

ብልፅግና ከገንዘብ ያለፈ ነው ፡፡ ብልፅግና የሚያስፈልገንን ገንዘብ ማግኘት ነው፡፡ ብልፅግና የሚያስፈልገንን አለማጣት ነው፡፡ የብልፅግና መገለጫዎች አንዱ ገንዘብ ቢሆንም የብልፅግና መገለጫዎች ግን በገንዘብ ብቻ አይወሰኑም፡፡
ገንዘብ የማይገዛቸው ብዙ ነገሮች አሉ፡፡ እንዲያውመ ውድ ነገሮች ገንዘብ ሊገዛቸው የሚችላቸው አይደሉም፡፡ በህይወታችን ውድ ነገሮች በነፃ የሚሰጡ ስጦታዎች ናቸው፡፡
ብልጥግና የሚገለጠባቸው አስራ አራቱ መንገዶች፡-
·         ብልፅግና ሃሳብን ማግኘት ነው፡፡
እግዚአብሄር መፈለግን በልባችን ያስቀምጣል፡፡ መፈለግና የልብ መነሳሳት የእግዚአብሄር ስጦታ ነው፡፡ ሁሉም ነገር ኖሮን ስለአንድ ነገር መፈለግን የልብ መነሳሳትን ካላገኘን ምንም ማድረግ አንችልም፡፡ አቅጣጫን ማግኘት ብልፅግና ነው፡፡
·         ብልጥግና ሰላም ማግኘት ነው፡፡
ሰው ሁሉንም ነገር አግኝቶ ሰላም ከሌለው ከዚያ ሰው ይበልጥ ደሃ ሰው የለም፡፡ ከእግዚአብሄር ጋር ሰላም የሆነ ሰው ባለጠጋ ሰው ነው፡፡ ከእግዚአብሄር ጋር ሰላም የሆነ ሰው ደግ ከሰው ጋር ሰላም ይኖረዋል፡፡
የሰው አካሄድ እግዚአብሔርን ደስ ያሰኘው እንደ ሆነ በእርሱና በጠላቶቹ መካከል ስንኳ ሰላምን ያደርጋል። ምሳሌ 16፡7
·         ብልፅግና ሰውን መውደድ ነው፡፡
የሰው ታላቅ ሃብት ሰው ነው፡፡ ምንም ያህል ገንዘብ ኖሮት ሰውን መውደድ የማይችል ሰው ባለጠጋ ሊባል አይችልም፡፡    
የጐመን ወጥ በፍቅር መብላት የሰባ ፍሪዳን ጥል ባለበት ዘንድ ከመብላት ይሻላል። ምሳሌ 15፡17
·         ብልፅግና እግዚአብሄርን መፍራት ነው፡፡
ከእግዚአብሄር ጋር እንዴት እንደምንኖር ከማወቅ በላይ ብልፅግና የለም፡፡ ለእግዚአብሄር የሚገባውን ክብር ከመስጠት በላይ ብልፅግና የለንም፡፡
የሚፈሩት አንዳችን አያጡምና ቅዱሳኑ ሁሉ፥ እግዚአብሔርን ፍሩት። መዝሙር 34፡9
·         ብልፅግና እረፍት ማግኘት ነው
እናንተ ደካሞች ሸክማችሁ የከበደ ሁሉ፥ ወደ እኔ ኑ፥ እኔም አሳርፋችኋለሁ። ቀንበሬን በላያችሁ ተሸከሙ ከእኔም ተማሩ፥ እኔ የዋህ በልቤም ትሑት ነኝና፥ ለነፍሳችሁም ዕረፍት ታገኛላችሁ፤ ማቴዎስ 11፡28-29
·         ብልፅግና ደስታ ነው
ሰው ሁሉ ነገር ኖሮት በህይወቱ ደስተኛ ካልሆነ ምን ይጠቅመዋል፡፡ እግዚአብሄር ደስታን ይሰጣል፡፡ እግዚአብሄር ቀለል አድርገን ማየት ያለብንን ቀለል አድርገን እንድናይ ያስችለናል፡፡ አንዳንድ ሰው ማግኘት መሰብሰብ እንጂ ያገኘውን ማጣጣም አያውቅም፡፡
እግዚአብሔር ለሰው ሁሉ ባለጠግነትንና ሀብትን መስጠቱ፥ ከእርስዋም ይበላና እድል ፈንታውን ይወስድ ዘንድ በድካሙም ደስ ይለው ዘንድ ማሠልጠኑ፤ ይህ የእግዚአብሔር ስጦታ ነው። መክብብ 5፡19
·         ብልፅግና እግዚአብሄርን መፈለግ  ነው
ባለጠጎች ደኸዩ፥ ተራቡም፥ እግዚአብሔርን የሚፈልጉት ግን ከመልካም ነገር ሁሉ አይጐድሉም። መዝሙር 34፡ 10
·         ብልፅግና ሰውን ማመን ነው፡፡
ሰውን ማመን የማይችል ሰው ባለጠጋ አይደለም፡፡ ካለሰው ምንም ማድረግ ስለማንችል ሰው ክዶትም ሆነ አታሎትም ሰውን እንደገና የሚያምን ሰው ባለጠጋ ነው፡፡
·         ብልፅግና መርካት ነው፡፡
ምንም ነገር ቢኖረው የማይረካ ሰው ባለጠጋ ሰው አይደለም፡፡ ባለው ምንም ነገር የሚረካ ሰው ደግሞ ደሃ ሊሆን አይችልም፡፡
ኑሮዬ ይበቃኛል ለሚለው ግን እግዚአብሔርን መምሰል እጅግ ማትረፊያ ነው፤ 1ኛ ጢሞቴዎስ 6፡6
·         ብልፅግና ካለምንም ብክነት ነገሮችን መጠቀም ነው
ብልፅጽግና ነገሮችን ማግኘት ብቻ ሳይሆን ነገሮች ሳይባክኑ ለታሰበላቸው አላማ መዋላቸው ብልፅግና ነው፡፡ ብዙ ነገር ኖሮት የሚያስተዳድርበት ጥበብ የሌለው ሰው ደሃ ሰው ነው፡፡
መንፈስ ይሙላባችሁ እንጂ በወይን ጠጅ አትስከሩ ይህ ማባከን ነውና፤ ኤፌሶን 5፡18
·         ብልፅግና ሞገስ ማግኘት ነው
ምንም ያህል ገንዘብ ቢኖረን በእግዚአብሄር ዘንድ ግን ተቀባይነት ካጣን ከዚህ በላይ ድህነት የለም፡፡ ምንም ያህል ገንዘብ ቢኖረን በሰው ፊት ሞገስ ተቀባይነት መወደድን ካላገኘን ምንም ማድረግ እንችልም፡፡ ምንም ሃብት ቢኖረን እንደራሱ አድርጎ በታማኝነትና በትጋት የሚሰራልን ሰው ከሌለን እንቀጭጫለን፡፡  
የአምላኬም እጅ በእኔ ላይ መልካም እንደሆነች፥ ንጉሡም የነገረኝን ቃል ነገርኋቸው። እነርሱም፦ እንነሣና እንሥራ አሉ። እጃቸውንም ለበጎ ሥራ አበረቱ። ነህምያ 2፡18
·         ብልፅግና የልብ ስፋት  ነው
ሰውን ይቅር የሚል የሚተው ምህረት የሚያደርግ ሰው ባለጠጋ ሰው ነው፡፡ ነገሮች ኖረውት ልቡ ቻይ ያልሆነ ሰው ግን ባለጠጋ ሰው አይደለም፡፡
እግዚአብሔርም ለሰሎሞን እጅግ ብዙ ጥበብና ማስተዋል በባሕርም ዳር እንዳለ አሸዋ የልብ ስፋት ሰጠው። 1ኛ ነገሥት 4፡29
·         ብልፅግና የምንሰራው ነገር ወደፍፃሜ መድረስ  ነው
እኔም መልሼ፦። የሰማይ አምላክ ያከናውንልናል፥ እኛም ባሪያዎቹ ተነሥተን እንሠራለን፤  ነህምያ 2፡20
·         ብልፅግና የእግዚአብሄር አብሮነት ነው
አቤቱ፥ ከሰዎች፥ እድል ፈንታቸው በሕይወታቸው ከሆነች ከዚህ ዓለም ሰዎች በእጅህ አድነኝ፤ ከሰወርኸው መዝገብህ ሆዳቸውን አጠገብህ፤ ልጆቻቸው ብዙ ናቸው የተረፋቸውንም ለሕፃናቶቻቸው ያተርፋሉ። እኔ ግን በጽድቅ ፊትህን አያለሁ፤ ክብርህን ሳይ እጠግባለሁ። መዝሙር 17፡14-15
ለተጨማሪ ፅሁፎች https://www.facebook.com/abiy.wakuma/notes
ለቪዲዮ መልእክቶች https://www.youtube.com/user/awordm/videos

#ኢየሱስ #ጌታ #ብልፅግና #የብልፅግናወንጌል #መፀለይ #ሞገስ #በረከት #ስኬት #እረኛእግዚአብሄር #ስምረት #መሰረታዊፍላጎት #ሁሉየእናንተነውና #ቤተክርስትያን #አማርኛ #ስብከት #መዳን #የተትረፈረፈህይወት #መፅሃፍቅዱስ #ሰላም #አቢይ #አቢይዋቁማ #አቢይዋቁማዲንሳ #መርካት #ደስታ #የልብስፋት #የእግዚአብሄርአብሮነት #እረፍት

No comments:

Post a Comment