Popular Posts

Saturday, April 15, 2017

ሞት - የተሸነፈ ጠላት

ሰው ሃጢያትን በሰራ ጊዜ ሞትን ሞተ ከእግዚአብሄር ተለያየ፡፡ ለሰው ከእግዚአብሄር ከመለየት በላየ የሞት ሞት የለም፡፡ ኢየሱስ ወደምድ የመጣው እኛን ወደ እግዚአብሄር ሊመልሰን ነው፡፡ ኢየሱስ በመስቀል ላይ የሰራውን ስራ ለእኔ ነው ብሎ የሚቀበል ሁሉ የዘላለም ህይወት ያገኛል፡፡ ለዘላለም ከእግዚአብሄር ጋር ይኖራል፡፡ ሰው ህይወት ከሆነው ከእግዚአብሄር ጋር ከተገናኘ ከለዚህ በኋላ የሚያስፈራው መንፈሱ ከስጋ የመለየት ነገር የለም፡፡
እንግዲህ ልጆቹ በሥጋና በደም ስለሚካፈሉ፥ እርሱ ደግሞ በሞት ላይ ሥልጣን ያለውን በሞት እንዲሽር፥ ይኸውም ዲያብሎስ ነው፥ በሕይወታቸውም ሁሉ ስለ ሞት ፍርሃት በባርነት ይታሰሩ የነበሩትን ሁሉ ነጻ እንዲያወጣ፥ በሥጋና በደም እንዲሁ ተካፈለ። ዕብራውያን 2፡14-15
ሞት ለዘመናት ሰዎችን በባርነት ቀንበር ይዞ ቆይቷል፡፡ ሰዎች ከሞት የሚያድናቸው አጥተው ተጨንቀዋል፡፡ ሰዎች ከሞት የሚያስጥላቸው ማንም አልነበረም፡፡  
በኢየሱስ ትንሳኤ ለመጀመሪያ ጊዜ ሞት ተሸነፈ፡፡ ሞት አቅሙን አጣው፡፡ ኢየሱስ ለመጀመሪያ ጊዜ ሞትን ድል ነሳው፡፡ ሞት ድል የተነሳው ለኢየሱስ ብቻ እለነበረም፡፡ በኢየሱስ የሚያምኑ ሁሉ ሞት እንዳይገዛቸው ነፃ ወጡ፡፡ አሁን ኢየሱስን የሚከተል ሞት ስጋቱ አይደለም፡፡    
ሞት ሆይ፥ መውጊያህ የት አለ? ሲኦል ሆይ፥ ድል መንሣትህ የት አለ? 1ኛ ቆሮንቶስ 15፡55
አሁን ሞት አያስፈራም፡፡ አሁን ሞት ሃይል የለውም፡፡ ሞት ተሸንፎዋል፡፡ ሞት በህይወት ተውጧል፡፡  
አሁን የዘላለም ህይወት ስላለን ሞት የምድር አገልግሎትን ጨርሰን የምንመረቅበት መንገድ ነው፡፡
በመሥዋዕት እንደሚደረግ፥ የእኔ ሕይወት ይሠዋልና፥ የምሄድበትም ጊዜ ደርሶአል። 2ኛ ጢሞቴዎስ 4፡6
ሞት በስጋ ውስጥ ከመኖር የምናርፍበት መንገድ ነው፡፡
በዚህ ውስጥ በእውነት እንቃትታለንና፥ ከሰማይም የሚሆነውን መኖሪያችንን እንድንለብስ እንናፍቃለንና 2 ቆሮንቶስ ሰዎች 5፡2
ሞት ከድንኳን ወደ እጅ ወዳልተሰራ ቤት የምንገባበት በር ነው፡፡
ድንኳን የሚሆነው ምድራዊ መኖሪያችን ቢፈርስ፥ በሰማይ ያለ በእጅ ያልተሠራ የዘላለም ቤት የሚሆን ከእግዚአብሔር የተሠራ ሕንጻ እንዳለን እናውቃለንና። 2ኛ ቆሮንቶስ 5፡1
ሞት በጊዜና በቦታ ከተወሰነው አለም ወዳልተወሰነውና ወደተሻለ አለም የምንገባበት መንገድ ነው፡፡
ልባችሁ አይታወክ፤ በእግዚአብሔር እመኑ፥ በእኔም ደግሞ እመኑ። በአባቴ ቤት ብዙ መኖሪያ አለ፤ እንዲህስ ባይሆን ባልኋችሁ ነበር፤ ስፍራ አዘጋጅላችሁ ዘንድ እሄዳለሁና፤ ዮሐንስ 14፡1-2
ሞት ጌታችንን የምናይበት ከጌታም ጋር ለዘላለም የምንኖርበት መንገድ ነው፡፡
በእነዚህም በሁለቱ እጨነቃለሁ፤ ልሄድ ከክርስቶስም ጋር ልኖር እናፍቃለሁ፥ ከሁሉ ይልቅ እጅግ የሚሻል ነውና፤ ፊልጵስዩስ 1፡23
በዚህ ውስጥ በእውነት እንቃትታለንና፥ ከሰማይም የሚሆነውን መኖሪያችንን እንድንለብስ እንናፍቃለንና 2ኛ ቆሮንቶስ ሰዎች 5፡2
ሞት የሚበሰብሰው የማይበሰብሰውን የሚለብስበት መንገድ ነው፡፡  
የዚያንም የመሬታዊውን መልክ እንደ ለበስን የሰማያዊውን መልክ ደግሞ እንለብሳለን። ዳሩ ግን ይህ የሚበሰብሰው የማይበሰብሰውን ሲለብስ ይህም የሚሞተው የማይሞተውን ሲለብስ፥ በዚያን ጊዜ፦ ሞት ድል በመነሣት ተዋጠ ተብሎ የተጻፈው ቃል ይፈጸማል። 1ኛ ቆሮንቶስ 15፡49፣54 
ለተጨማሪ ፅሁፎች https://www.facebook.com/abiy.wakuma/notes
ለቪዲዮ መልእክቶች https://www.youtube.com/user/awordm/videos

#ኢየሱስ #ጌታ #ህይወት #ፋሲካ #ትንሳኤ #ሞት #አማርኛ #ስብከት #መዳን #መፅሃፍቅዱስ #መንፈስቅዱስ #ማለፍ #ፌስቡክ #አቢይዋቁማ #አቢይዋቁማዲንሳ  

No comments:

Post a Comment