Popular Posts

Tuesday, April 25, 2017

የሰውና የሰይጣን ሃሳብ

ሰው ለእግዚአብሄር ክብር ስለተፈጠረ ለእግዚአብሄር ክብር ካልኖረ በሰይጣን ተገዝቷል ማለት ነው፡፡ ብዙ ጊዜ ሰዎች የሚታለሉት ቀንድ ያበቀለ አውሬ አይነት ሰይጣን በህይወታቸው ካልመጣ ከሰይጣን ጥቃት ነፃ እንደሆኑ ስለሚመስላው ነው፡፡ ሰይጣን የሚሰራው በግልፅ አይደለም፡፡ ሰይጣን የሚሰራው በማታለል ነው፡፡ በሰው ስጋ የሚሰራው ሰይጣን ነው፡፡ በሰው ምኞት የሚሰራው ሰይጣን ነው፡፡ የስጋችንንና የልቦናችንን ፈቃድ ካደረግን በሰይጣን ፈቃድ እየተመላለስን ነው፡፡
በእነርሱም፥ በዚህ ዓለም እንዳለው ኑሮ፥ በማይታዘዙትም ልጆች ላይ አሁን ለሚሠራው መንፈስ አለቃ እንደ ሆነው በአየር ላይ ሥልጣን እንዳለው አለቃ ፈቃድ፥ በፊት ተመላለሳችሁባቸው። በእነዚህም ልጆች መካከል እኛ ሁላችን ደግሞ፥ የሥጋችንንና የልቡናችንን ፈቃድ እያደረግን፥ በሥጋችን ምኞት በፊት እንኖር ነበርን ኤፌሶን 2፡1-3
በምድር ላይ ሁለት አይነት ሃሳብ ብቻ ነው ያለው፡፡ የእግዚአብሄር ሃሳብ አለ፡፡ የእግዚአብሄር ያልሆነ ሃሳብ አለ፡፡ የእግዚአብሄር ያልሆነው ሃሳብ ሁሉ የሰው ሃሳብ ነው የሰይጣንም ሃሳብ ነው፡፡
በምድር ላይም ያለው ጥበብ ሁለት አይነት ጥበብ ነው፡፡ የእግዚአብሄር ጥበብ አለ፡፡ የእግዚአብሄር ያልሆነ ጥበብ አለ፡፡ ይህ የእግዚአብሄር ያልሆነው ጥበብ የሥጋና የአጋንንትም ጥበብ ነው፡፡
ነገር ግን መራራ ቅንዓትና አድመኛነት በልባችሁ ቢኖርባችሁ፥ አትመኩ በእውነትም ላይ አትዋሹ። ይህ ጥበብ ከላይ የሚወርድ አይደለም፤ ነገር ግን የምድር ነው፥ የሥጋም ነው፥ የአጋንንትም ነው፤ ያዕቆብ 3፡14-15
ሰይጣን እፃን ለማጥቃት የሚጠቀመው የስጋን ሃሳብ ተጠቅሞ ነው፡፡ ሰይጣን እኔ ሰይጣን ነኝ ብሎ ሳይሆን የሚመጣው ለሰው ስጋ በሚመች ሃሳብ ነው፡፡
ኢየሱስ ጴጥሮስን አንተ ሰይጣን ብሎ የሰውን እንጂ የእግዚአብሔርን አታስብምና ብሎ ሲገስፀው እናያለን፡፡ ሰው ከእግዚአብሄር ጋር ለመተላለፍ የሰይጣንን ሃሳብ ማሰብ የለበትም፡፡ ሰው የሰውን ሃሳብ ካሰበ በተዘዋዋሪ የሰይጣንን ሃሳብ አሰበ ማለት ነው፡፡ ሰይጣን እኔ ሰይጣን ነኝ አገልግሉኝ ብሎ ሳይሆን የሚመጣው የራስ ወዳድነትን ሰውኛን ሃሳብ እንድናስብ በማድረግ ነው፡፡
እርሱ ግን ዘወር ብሎ ጴጥሮስን፦ ወደ ኋላዬ ሂድ፥ አንተ ሰይጣን፤ የሰውን እንጂ የእግዚአብሔርን አታስብምና ዕንቅፋት ሆነህብኛል አለው። ማቴዎስ 16፡23
እግዚአብሄር በፍጹም ልባችን በፍጹም ነፍሳችን በፍጹም ኃይላችን በፍጹም አሳባችን እንድንወደው ስለሚፈልግ ራስ ወዳድነት ካለብን በተዘዋዋሪ ሰይጣንን እያገለገልን ነው እንጂ እግዚአብሄርን እየወደድን አይደለም፡፡
ዓለምን በሚወድ ውስጥ የአባት ፍቅር በእርሱ ውስጥ የለም የሚለው ለዚህ ነው፡፡ አለምን መውደድ በተዘዋዋሪ ሰይጣንን ማገልገል ነው፡፡
ማንም ዓለምን ቢወድ የአባት ፍቅር በእርሱ ውስጥ የለም። 1ኛ ዮሐንስ 2፡15
በህይወታችን ያለውን የእግዚአብሄርን አላማ ለመሳት የሰይጣን አምላኪ መሆን የለብንም ከእግዚአብሄር ጋር ለመተላለፍ እንደሰው ልማድ መመላለስ ይበቃናል፡፡  
ገና ሥጋውያን ናችሁና እስከ አሁን ድረስ ገና አትችሉም። ቅናትና ክርክር ስለሚገኝባችሁ ሥጋውያን መሆናችሁ አይደላችሁምን? እንደ ሰው ልማድስ አትመላለሱምን? 1 ቆሮንቶስ 3፡3
ለተጨማሪ ፅሁፎች https://www.facebook.com/abiy.wakuma/notes
ለቪዲዮ መልእክቶች https://www.youtube.com/user/awordm/videos

#ኢየሱስ #ጌታ #ሰይጣን #ዲያብሎስን #ሽንገላ #ሃሳብ #የስጋፈቃድ #የልቦናፈቃድ #ምኞት #አእምሮ #ልብ #ኢየሱስ #ጌታ #መፅሃፍቅዱስ #ቤተክርስትያን #አማርኛ #አቢይዋቁማ #አቢይዋቁማዲንሳ #ስብከት #እምነት #ነፃነት #መስማት #መከተል #አቢይ #አቢይዋቁማ #አቢይዋቁማዲንሳ

No comments:

Post a Comment