Popular Posts

Wednesday, April 19, 2017

እኔም አሳርፋችኋለሁ ፣ ለነፍሳችሁም ዕረፍት ታገኛላችሁ፤

እናንተ ደካሞች ሸክማችሁ የከበደ ሁሉ፥ ወደ እኔ ኑ፥ እኔም አሳርፋችኋለሁ። ቀንበሬን በላያችሁ ተሸከሙ ከእኔም ተማሩ፥ እኔ የዋህ በልቤም ትሑት ነኝና፥ ለነፍሳችሁም ዕረፍት ታገኛላችሁ፤ ቀንበሬ ልዝብ ሸክሜም ቀሊል ነውና። ማቴዎስ 11፡28-30
እግዚአብሄር ለሰው ልጅ የሚያስፈልጉትን ነገሮች ሁሉ በአምስት ቀን ፈጠረ፡፡ እግዚአብሄር በሰባተኛው ቀን ከማረፉ አንድ ቀን ቀደም ብሎ ሰውን በስድስተኛው ቀን ፈጠረው፡፡ ሰው የተፈጠረው እንዲያርፍ ነው፡፡ ሰው ዲዛይን የተደረገውና የተሰራው ለእረፍት ነው፡፡ ለዚህ ነው ሰው ካላረፈ የሚጨነቀውና ፣ የሚጎሳቆለውና የሚታመመው፡፡ አለማረፍ ጤና አይደለም፡፡ አለማረፍ የነገሮች መዛባት ምልክት ነው፡፡
ኢየሱስም ወደምድር ሲመጣ ቃል የገነባው እረፍት ነው፡፡ ወደ ኢየሱስ በመምጣት ከነፍስ ጭንቀትና ከሰቆቃ ህይወት ማረፍ ይቻላል፡፡
ሰው የሚያርፈው በእግዚአብሄር ላይ ሲታመን ብቻ ነው፡፡ ሰው እንዳያርፍ የሚነዘንዙት ነገሮች ዙሪያውን ሳላሉ ሰው በእግዚአብሄር ላይ ካልተደገፈ አያርፍም፡፡  
ሰው ለማረፍ በእግአብሄር ላይ ቃል ላይ መታመን አለበት፡፡ ለእግዚአብሄር ቃል የዋህ ያልሆነ የእግዚአብሄርን ቃል በሞኝነት የማይቀበል ሰው ሊያርፍ አይችልም፡፡ እግዚአብሄርን ለማመን የሚቸግረው ሰው ሊያርፍ አይችልም፡፡ እግዚአብሄር በቃሉ የተናገረውን እንዳለ የማይቀበል ሰው ከእረፍት ይጎድላል፡፡
አንድ መክሊትም የተቀበለው ደግሞ ቀርቦ፦ ጌታ ሆይ፥ ካልዘራህባት የምታጭድ ካልበተንህባትም የምትሰበስብ ጨካኝ ሰው መሆንህን አውቃለሁ፤ ፈራሁም ሄጄም መክሊትህን በምድር ቀበርሁት፤ እነሆ፥ መክሊትህ አለህ አለ። ማቴዎስ 25፡24-25
እግዚአብሄር በእርሱ ላይ ያለው አላማ ፍቅር መሆኑ ያልተረዳ ሰው ካለ እረፍት ዘመኑን ይፈጃል፡፡
ወደ ወይን ጠጁም ቤት አገባኝ፥ በእኔ ላይ ያለው ዓላማውም ፍቅር ነው። መኃልየ መኃልይ 2፡4
ለእናንተ የማስባትን ሃሳብ እኔ አውቃለሁና ያለውን እግዚአብሄርን በየዋህነት የማይቀበል ሰው ዘመኑ ይባክናል፡፡
ለእናንተ የማስባትን አሳብ እኔ አውቃለሁ፤ ፍጻሜና ተስፋ እሰጣችሁ ዘንድ የሰላም አሳብ ነው እንጂ የክፉ ነገር አይደለም። ኤርምያስ 29፡11
የሚያስጨንቃችሁን በእርሱ ላይ ጣሉት እርሱ ስለእናንተ ያስባልና ለሚለው ቃል የዋህ የማይሆን ሰው በዘመኑ ሊያርፍ በፍፁም አይችልም፡፡  
ሰው ትሁት ካልሆነ ለእግዚአበሄር አሰራት ጊዜል ካልሰጠ ሊያርፍ አይችልም፡፡  
ኢየሱስ የየዋህነትና የእረፍት ምሳሌ ነው፡፡ ኢየሱስ በአብ ተልኮ ራሱን ባዶ አደረገ፡፡ በምድር ላይ በአግዚአብሄር ፊት በሁሉ በሁሉ ትሁት ሆነ፡፡ ለእግዚአብሄር ሃሳብ ሁሉ የዋህ ሆነ፡፡ በእግዚአብሄር ስለታመነ በሁሉ እግዚአብሄርን ታዘዘ፡፡ እስከመስቀል ሞት ድረስ የታዘዘ ሆነ፡፡
ከእኔም ተማሩ፥ እኔ የዋህ በልቤም ትሑት ነኝና፥ ለነፍሳችሁም ዕረፍት ታገኛላችሁ፤ ማቴዎስ 11፡29
ለተጨማሪ ፅሁፎች https://www.facebook.com/abiy.wakuma/notes
ለቪዲዮ መልእክቶች https://www.youtube.com/user/awordm/videos
#እረፍት #ቅድሚያ #እምነት #መደገፍ #ሰንበት #አስቀድማችሁ #ፅድቁን #ኢየሱስ #ክርስቶስ #ጌታ #ቤተክርስትያን #አማርኛ #ስብከት #እምነት #መፅሃፍቅዱስ #መንፈስቅዱስ #ምህረት #ፌስቡክ #አቢይዋቁማ #አቢይዋቁማዲንሳ


No comments:

Post a Comment