Popular Posts

Thursday, March 30, 2017

መጋቢነትና የገቢ ምንጭ

ለቤተክርስቲያነ ከተሰጡት 5ቱ የአገልግሎትር ስጦታዎች አንዱ መጋቢነት ነው፡፡ መጋቢነት ለሰዎች ነፍስ የመትጋት ታላቅ ሃላፊነትን የሚጠይቅ አገልግሎት ነው፡፡
የመጋቢነትን አገልገሎት ዋጋ ሊከፍል የሚችል ገንዘብ የለም፡፡ መጋቢ በምድር ላይ እንደሚኖር እንደ ማንኛውም ሰው ገንዘብ በምድር ላይ ኑሮ ያስፈልገዋል፡፡ መፅሃፍ ቅዱስም ስለ መጋቢ ብሎም ስለሌሎች የአገልግሎት ስጦታዎች የገቢ ምንጭ ያስተምራል፡፡
መፅሃፍ ቅዱስ በኑሮ ሃሳብና በባለጠግነት ምኞት ሙሉ ፍሬ ስለማያፈሩ ሰዎች ስለሚያስተምር መጋቢም ሙሉ ፍሬ እንዳያፈራ ከሚያደርጉት ነገሮች ራሱን ሊጠብቅ ይገባዋል፡፡(ማርቆስ 4፡19) መጋቢ የገቢ ምንጩን ከየት ያገኛል፡፡ መጋቢ ስለገቢ ምንጩ ዘወር ማለት ያለበት ወደ ማን ነው?
1.      መጋቢ ለአቅርቦቱ ወደ እግዚአብሄር ብቻ ማየት ይገባዋል 
መጋቢ በመጀመሪያ የእግዚአብሄር ልጅ ነው፡፡ የእግዚአብሄር ልጅ የሆነ ሰው ሁሉ ደግሞ የሚኖረው ስለሰራ ወይም ስላልሰራ አይደለም፡፡ የእግዚአብሄርን ፅድቅና መንግስቱን እሰከፈለገ ድረስ እግዚአብሄር የሚያስፈልገውን የሚሰጠውና የሚንከባከበው የቤተሰቡን አባል ስለሆነ ብቻ ነው፡፡
ነገር ግን አስቀድማችሁ የእግዚአብሔርን መንግሥት ጽድቁንም ፈልጉ፥ ይህም ሁሉ ይጨመርላችኋል። ማቴዎስ 6፡33
በቤት የተወለደ ልጅን አባቱ የሚንከባከበው እንደስራው መጠን ሳይሆን እንደ ቤተሰቡ ደረጃ ነው፡፡ እንዲሁም መጋቢ የመጋቢነትን ታላቅ ሃላፊነት ከመቀበሉ በፊት የልጅነት መብት የመጠቀም እምነት ያስፈልገዋል፡፡ መጋቢ ከመሆኑ በፊት በእግዚአብሄርን አባትነትና አቅራቢነት እምነት ሊኖረው ያስፈልጋል፡፡ ወደ መጋቢነቱ አገልግሎት ከመግባቱ በፊት ስለሚያስፈልገው ነገር እግዚአብሄርን ማመን ሊማር ይገባዋል፡፡
2.     መጋቢ ህዝቡን የገቢ ምንጭ ማድረግ የለበትም፡፡

መጋቢ የአቅርቦት ምንጩ እግዚአብሄርን ብቻ ማድረግ አለበት፡፡ መጋቢ የሚመግባቸውን ሰዎች ምንጩ ካደረገ ህይወቱ ይወሳሰባል ነፃም ሊሆን አይችልም፡፡ ሰው ሲቀንስና ሲጨምር ገቢው አብሮ ይጨምራል ይቀንሳል፡፡ እግዚአብሄር የሰጠውን የመጋቢነት ሃላፊነት ለመወጣት ሳይሆን ገቢውን ለመጨመር በምንም መልኩ ህዝብን ለማብዛት ይፈተናል፡፡ መጋቢ የሚመራቸውን ሰዎች የገቢ ምንጩ ካደረገ እንደ ገቢው አመጣጥ ከፍ ዝቅ እንዳይል ብዙ ገንዘብ ያላቸውን ልዩ እንክብካቤ ለማድረግ ይፈተናል፡፡ መጋቢ እግዚአብሄርን የገቢ ምንጩ ካላደረገ የሚመራቸውን ለመገሰፅ አቅም ያጣል፡፡ መጋቢ ህዝቡን የገቢ ምንጩ ካደረገ የእግዚአብሄርን ቃል ለማመቻመች ይፈተናል፡፡     

3.     መጋቢ ስለ አቅራቦቱ የእግዚአብሄርን ቃል ማመን አለበት

መጋቢዎች የእግዚአብሄር ቃል የሚናገረውን ወንጌልን የሚሰራ በወንጌል ይኖር የሚለውን ቃል ለማመን ሲቸገሩ ሌላ የገቢ ምንጭ ለመፍጠር ይጥራሉ፡፡ ሌላ የገቢ ምንጭ መፍጠር በራሱ ችግር የለውም፡፡ አንዳንዶች መጋቢዎች ለቃሉና ለፀሎት ከመትጋት ውጭ ሌላ ስራ እየሰሩ የእግዚአብሄን ህዝብ የሚያገለግሉ የተባረኩ መጋቢዎች አሉ፡፡

ችግሩ መጋቢው ወንጌልን በሚሰራበት ጊዜና ጉልበት ሌላ የገቢ ምንጭ ማስገኛ ነገር ውስጥ ከገባ የሰዎችን ህይወት በትጋት የመስራት ስራው ይበደላል፡፡ መፅሃፍ ወንጌልን የሚሰራ በወንጌል ይኑር ያለው መጋቢው ለቃልና ለፀሎት እንዲተጋ ሌላ ጊዜውንና ጉልበቱን የሚከፋፈል ነገር ውስጥ እንዳይገባ ነው፡፡

ከዚህ አንፃር መጋቢው ያለበትን ጫና ለመቀነስ የሚማረው ከሚያስተምረው ጋር መልካሙን ነገር ሁሉ መከፋፈል አለበት፡፡

ነገር ግን ቃሉን የሚማር ከሚያስተምረው ጋር መልካምን ነገር ሁሉ ይከፋፈል። ገላትያ 6፡6

እንዲሁም መጋቢዎች መንፈሳዊውን ነገር ዘርተው ከሚያገለግሉዋቸው ስጋዊን ነገር ቢያጭዱ ትልቅ ነገር አይደለም፡፡  

እኛ መንፈሳዊን ነገር የዘራንላችሁ ከሆንን የእናንተን የሥጋዊን ነገር እኛ ብናጭድ ትልቅ ነገር ነውን? 1ኛ ቆሮንቶስ 9፡11

ለተጨማሪ ፅሁፎች https://www.facebook.com/abiy.wakuma/notes
ለቪዲዮ መልእክቶች https://www.youtube.com/user/awordm/videos

#ኢየሱስ #ጌታ #እምነት #አቅርቦት #አማርኛ #ስብከት #መዳን #መፅሃፍቅዱስ #ልብ #ገቢ #ቃል #መዝራት #ወንጌል #መጋቢ #ደስታ #አቢይ #አቢይዋቁማ #አቢይዋቁማዲንሳ

No comments:

Post a Comment