Popular Posts

Monday, March 20, 2017

እንደ እግዚአብሄር ፈቃድ የመለመን ድፍረት

በእርሱ ዘንድ ያለን ድፍረት ይህ ነው፤ እንደ ፈቃዱ አንዳች ብንለምን ይሰማናል። የምንለምነውንም ሁሉ እንዲሰማልን ብናውቅ ከእርሱ የለመነውን ልመና እንደ ተቀበልን እናውቃለን። 1ኛ ዮሐንስ 5፡14-15
በህይወታችን የፀሎትን ቃል ለማውጣት እጅግ መቸኮል የለብንም፡፡ ፀሎት በመረጋጋት ሊሆን ይገባዋል፡፡ የፀሎትን ቃል ከማውጣታችን በፊት የፀሎት መሰረት መሰራት አለበት፡፡ ይህ የፀሎት መሰረት የእግዚአብሄር ፈቃድ ነው፡፡
እግዚአብሄር የማይሰማው ፀሎት አለ፡፡ እግዚአብሄር የሚሰማ ፀሎት አለ፡፡
የሚሰማን ፀሎት ለመፀለይ የእግዚአብሄርን ፈቃድ ማግኘት ይገባናል፡፡ የእግዚአብሄርን ፈቃድ ሳናውቅ መፀለይ ጉምን እንደመዝገን ነው፡፡ የእግዚአብሄርን ፈቃድ ከቃሉ ፈልገን ለማግኘት ካልተጋን የእግዚአብሄርን ፈቃድ መፀለይ አንችልም፡፡ የፀሎት ቃልን ከማውጣታችን በፊት የሚቀድመው የእግዚአብሄርን ፈቃድ መረዳት ነው፡፡ የእግዚአብሄርን ፈቃድ መረዳት የምንችለው ደግሞ ከእግዚአብሄር ቃል ብቻ ነው፡፡
በምንፀልየው ፀሎት ፊት እንደ ፈቃድህ የሚል ንግግር ማስገባት የእግዚአብሄርን ፈቃድ ፈልጎ ላለማግኘት በቂ ምክኒያት አይደለም፡፡ እንደ ፈቃድህ ይህን አድርግልኝ እንደ ፈቃድህ ያንን አድርግልኝ ከማለት ፈቃዱን ፈልጎ በማግኘት እንደፈቃዱ መለመን የለመንነውን እንደሰማን እንድናውቅ ያደርገናል፡፡ እንዲሁም የለመንነውን እንደተቀበልን እናውቃለን፡፡
የፀሎት ዋናው ክፍል የፀሎት ቃልን መናገር አይደለም፡፡ የፀሎት ዋናው ክፍል የእግዚአብሄርን ፈቃድ መረዳት ነው፡፡ የእግዚአብሄርን ፈቃድ ከእግዚአብሄር ቃል ውስጥ ፈልገን ካገኘን የፀሎት ትልቁ ስራችን ተሰራ ማለት ነው፡፡ በፀሎታችን የእግዚአብሄርን ፈቃድ እንድንፀልይ እንዲረዳን መንፈስ ቅዱስን መጠበቅ አለብን፡፡
እንዲሁም ደግሞ መንፈስ ድካማችንን ያግዛል፤ እንዴት እንድንጸልይ እንደሚገባን አናውቅምና፥ ነገር ግን መንፈስ ራሱ በማይነገር መቃተት ይማልድልናል፤ ሮሜ 8፡26
እንደ ፈቃዱ ከፀለይን እግዚአብሄር እንደሚሰማን እናውቃለን፡፡ እግዚአብሄር ከሰማን የለመንነውን እንደተቀበልን እናውቃለን፡፡ የእግዚአብሄርን ፈቃድ አግኝተን ከፀለይን መልሱ እጃችን ከመግባቱ በፊት ማመስገን እንችላለን፡፡  
 ይህን ፅሁፍ ለሌሎች ሼር   share ማድረግ ቢወዱ
ለተጨማሪ ፅሁፎች https://www.facebook.com/abiy.wakuma/notes
ለቪዲዮ መልእክቶች https://www.youtube.com/user/awordm/videos

#ኢየሱስ #ጌታ #የእግዚአብሄርፈቃድ #ፀሎት #ልመና #እንዲሰማን #ቤተክርስትያን #አማርኛ #የእግዚአብሄርቃል #መፅሃፍቅዱስ #ሰላም #አቢይ #አቢይዋቁማ #አቢይዋቁማዲንሳ #መጠየቅ #መንበርከክ #ምስጋና 

No comments:

Post a Comment