Popular Posts

Wednesday, January 18, 2017

የየዋህነት ክብር

የጌታም ባሪያ ለሰው ሁሉ ገር ለማስተማርም የሚበቃ ለትዕግሥትም የሚጸና ሊሆን እንጂ ሊጣላ አይገባውም። ደግሞም፦ ምናልባት እግዚአብሔር እውነትን ያውቁ ዘንድ ንስሐን ይሰጣቸዋልና ፈቃዱን ለማድረግ በዲያብሎስ ሕያዋን ሆነው ከተያዙበት ወጥመድ ወጥተው፥ ወደ አእምሮ ይመለሳሉ ብሎ የሚቃወሙትን በየዋህነት ይቅጣ። 2ኛ ጢሞቴዎስ 2፡24-26
የዋህነት የመንፈስ ፍሬ እንደሆነና መንፈሳዊ ውጤታችንና ፍሬያማነታችነ የሚለካበት ወሳኝ ባህሪ እንደሆነ መፅሃፍ ቅዱስ ያስተምራል፡፡
የመንፈስ ፍሬ ግን ፍቅር፥ ደስታ፥ ሰላም፥ ትዕግሥት፥ ቸርነት፥ በጎነት፥ እምነት፥ የውሃት ራስን መግዛት ነው። ገላትያ 5፡22
በነገር ሁሉ ምሳሌያችን የሆነው ኢየሱስ የዋህ ነበረ፡፡ ከእኔም ተማሩ ብሎ ያስተምረናል፡፡ 
ቀንበሬን በላያችሁ ተሸከሙ ከእኔም ተማሩ፥ እኔ የዋህ በልቤም ትሑት ነኝና፥ ለነፍሳችሁም ዕረፍት ታገኛላችሁ፤  ማቴዎስ 11፡29
የዋህነት የጥሪያችን ደረጃ ነው፡፡ ከየዋህነት ያነሰ ኑሮ እንድንኖር አልተጠራንም፡፡  ለጥሪያችን እንደሚገባ መኖር በየዋህነት መኖር ነው፡፡
እንግዲህ በጌታ እስር የሆንሁ እኔ በተጠራችሁበት መጠራታችሁ እንደሚገባ ትመላለሱ ዘንድ እለምናችኋለሁ፤ በትሕትና ሁሉና የዋህነት በትዕግሥትም፤ እርስ በርሳችሁ በፍቅር ታገሡ፤ ኤፌሶን 4፡1-2
ስለየዋህነት መፅሃፍ ቅዱስ ብዙ ያስተምራል፡፡ ለምሳሌ ያህል ይህን ያህል ስለ የዋህነት አስፈላጊነት ካየን የየዋህነትን ትርጉም እንመልከት፡፡
ግን የዋህነት ምንድነው?
የዋህነት በብዙ ቃላት ሊተረጎም የሚችል ቃል ነው፡፡ የየዋህነትን ትርጉም እንመልከት፡-
ቸር
መልካምና ርህሩህ አዛኝ ስለሌላው ግድ የሚለው
ክፉና ግፈኛ ያልሆነ  
ለሰው የሚጠነቀቅ ፣ ግዴለሽ ያልሆነ ፣ ራስ ወዳድ ያልሆነ ፣ የሰውን ፍላጎት የሚያከብር
ልከኛ  
ለጥቅም የማይስገበገብ ፣ በቃኝ የሚል ፣ ለመኖር ብዙ ነገር የማይጠይቅ
የተከበረ  
ሰዎች የሚያከብሩት ፣ ክብሩን ጠብቆ የሚኖር ፣ የሚያዋርደውንና የሚያስንቀውን ክፉ ነገር የማያደርግ
ጨዋ
የተገራ ፣ ለጥቅም የማይጣላ ፣ በራስ ወዳድነት የማይከራከር
ሰላማዊ
ሰላም ያለው ፣ ለሌላም ሰላም የሚሰጥ ፣ አስጊ ያልሆነ
አክባሪ
ሰውን አክባሪ ፣ ሰውን የማይንቅ ፣ ለሰው ትልቅ ስፍራ ያለው
ጭምት
ረጋ ያለ ፣ የማይቸኩል ፣ ቁጥብ ፣ ስሜቱን የሚገዛ
በተራ ነገር ላይ የማይገኝ
በትክክለኛው መንገድ የማይመጣን ጥቅም የሚንቅ ፣ ነውረኛ ረብ የማይወድ
ደረጃው ከፍ ያለ
መልካም ባህሪ ያለው በሚሉት ቃላት ሊገለፅ ይችላል፡፡
በጣም ልቤን የነካኝ ይህን ሁሉ ሃሳብ ይበልጥ ሊገልፅ የሚችል የሚርያም ዌብስተር የመዝገበ ቃላት ትርጉምን ላካፍላችሁ፡፡  
Gentleman a :  a man of noble or gentle birth d :  a man of independent means who does not engage in any occupation or profession for gain  
Gentleman የዋህ ፡- የነገስታት ቤተሰብ አባል የሆነ ጥቅም ለማግኘት ማንኛውንም ሥራ ወይም ሙያ ለመሰማራት የማይፈልግ ነፃ ሰው ማለት ነው፡፡
እኛ ኢየሱስን አንደአዳኝና ጌታ የተቀበልን ክርስቲያኖች ይህ መግለጫ በትክክል ይገልጠናል፡፡ አሁን የእግዚአብሄር ልጆች ሆነናል፡፡ የምንሰራው ለመኖር አይደለም፡፡ ለመኖር አንጨነቅም፡፡ ለኑሮዋችን የሚያስፈልገውን ነገር ሁሉ የሚያዘጋጀው አባታችን እግዚአብሄር ነው፡፡
እኛ የምንሰራው ከፍ ላለ ነገር ነው፡፡እኛ የምንሰራው ለመንግስቱ ነው፡፡ እኛ የምንፈልገው የእግዚአብሄርን ፅድቅ ነው፡፡ ሌላ ሁሉ በእግዚአብሄር የሚጨመርልን የእግዚአብሄር ቤተሰብ አባላት ነን፡፡
እንግዲህ፦ ምን እንበላለን? ምንስ እንጠጣለን? ምንስ እንለብሳለን? ብላችሁ አትጨነቁ፤ ይህንስ ሁሉ አሕዛብ ይፈልጋሉ፤ ይህ ሁሉ እንዲያስፈልጋችሁ የሰማዩ አባታችሁ ያውቃልና። ነገር ግን አስቀድማችሁ የእግዚአብሔርን መንግሥት ጽድቁንም ፈልጉ፥ ይህም ሁሉ ይጨመርላችኋል። ማቴዎስ 6፡31-33
ለተጨማሪ ፅሁፎች https://www.facebook.com/abiy.wakuma/notes
ለቪዲዮ መልእክቶች https://www.youtube.com/user/awordm/videos


No comments:

Post a Comment