Popular Posts

Friday, October 21, 2016

የዘላለምን ሕይወት ያዝ

መልካሙን የእምነት ገድል ተጋደል፥ የተጠራህለትንም በብዙም ምስክሮች ፊት በመልካም መታመን የታመንህለትን የዘላለምን ሕይወት ያዝ። 1ኛ ጢሞቴዎስ 6፡12
የዘላለም ህይወት የእግዚአብሄር ታላቅ ስጦታ ነው፡፡ ይህን ታላቅ ስጦታ እንደመቀበላችን መጠን ህይወታችን ሁሉ በዚያ ስጦታ መቃኘት አለበት፡፡
ምንም ነገር ስናስብ ከዘላለማዊ ህይወት እይታ እንፃር ማሰብ አለብን ፣ ምንም ነገር ስንወስን ከዘላለም ህይወት አንፃር ልንወስን ይገባል ፣ ምንም ነገር ስናደርግ ዘላለም እንደሚኖር ሰው ማድረግ አለብን፡፡
በነጻነት ሕግ ፍርድን ይቀበሉ ዘንድ እንዳላቸው ሰዎች እንዲህ ተናገሩ፥ እንዲህም አድርጉ። ያዕቆብ 2፡12
ሰው ዘላለማዊ ህይወትን ካልያዘና የሚያደርገውን ሁሉ ከዘላለማዊ ህይወት አንፃር ካልመዘነውና ካላደረገው እይታው የቅርብና የአሁኑን ብቻ ያያል፡፡
እነሆም፥ ሐሜትና ደስታ በሬውንና በጉንም ማረድ ሥጋንም መብላት የወይን ጠጅንም መጠጣት ሆነዋል፤ እናንተ፦ ነገ እንሞታለንና እንብላ እንጠጣ ብላችኋል። ኢሳይያስ 22፡13
ሰው ትክክለኛ እይታ አለው የሚባለው ነገሮችን ሁሉ በዘላለም እይታ ማየት ሲችል ብቻ ነው፡፡ እይታው ዘላለምን ካላሳየው የቅርቡን ብቻ የሚያይ እውር ሰው ነው፡፡
እነዚህ ነገሮች የሌሉት ዕውር ነውና፥ በቅርብም ያለውን ብቻ ያያል፥ የቀደመውንም ኃጢአቱን መንጻት ረስቶአል። 2ኛ ጴጥሮስ 1፡9
ከምድር ምንም አይነት ስኬትና ክንውን ጋር ሲነፃፀር የዘላለምን ህይወት የሚያክለው የለም፡፡ በእይታችን የዘላለም ህይወት ከሌለና እግዚአብሄርን ተስፋ ያደረግነው ለዚህ ለምድራዊ ህይወት ብቻ ከሆነ ምስኪኖች ነን፡፡
በዚች ሕይወት ብቻ ክርስቶስን ተስፋ ያደረግን ከሆነ፥ ከሰው ሁሉ ይልቅ ምስኪኖች ነን። 1ኛ ቆሮንቶስ 15፡19
እያንዳንዱ እርምጃችን ዘላለም ለሚኖር ሰው የሚገባ መሆን አለበት፡፡ ከምንም ነገር በላይ የዘላለምን ህይወት በትጋት መጠባበቅ አለብን፡፡ እኛ አገራችን በሰማይ ነውና፥ ከዚያም ደግሞ የሚመጣ መድኃኒትን እርሱንም ጌታን ኢየሱስ ክርስቶስን እንጠባበቃለን፤ ፊልጵስዩስ 3፡20
በምድር ላይ የምናደርገው ማንኛውም ነገር በነፃነት ህግ እንደሚፈረድባቸው በጌታ ዙፋን ፊት እንደሚቀርቡ ሰዎች መሆን ይኖርበታል፡፡
እንግዲህ ከክርስቶስ ጋር ከተነሣችሁ፥ ክርስቶስ በእግዚአብሔር ቀኝ ተቀምጦ ባለበት በላይ እሹ፤ በላይ ያለውን አስቡ እንጂ በምድር ያለውን አይደለም። ሞታችኋልና፥ ሕይወታችሁም በእግዚአብሔር ከክርስቶስ ጋር ተሰውሮአልና፤ ሕይወታችሁ የሆነ ክርስቶስ በሚገለጥበት ጊዜ፥ በዚያን ጊዜ እናንተ ደግሞ ከእርሱ ጋር በክብር ትገለጣላችሁ። ቆላስይስ 3፡1-4
ይህን ፅሁፍ ለሌሎች ሼር share ማድረግ ቢወዱ
ለተጨማሪ ፅሁፎች https://www.facebook.com/abiy.wakuma/notes
#የዘላለምህይወት #ሰማይ #ዘላለም #ኢየሱስ #ጌታ #መሪነት #ቤተክርስትያን #አማርኛ #ስብከት #መዳን #መፅሃፍቅዱስ #መጋቢ #እምነት #ተስፋ #ፍቅር #ጌታ #ሰላም #ደስታ #አቢይ #አቢይዋቁማ #አቢይዋቁማዲንሳ #እወጃ #መናገር #ፅናት #ትግስት #መሪ

No comments:

Post a Comment