Popular Posts

Thursday, September 29, 2016

እምነት አሁን ነው

ስለእምነት አስፈላጊነት ተናግረን አናበቃም፡፡ ምክኒያቱም ምንም ምንም ብናደርግ የምናደርገው ሁሉ በእምነት መሆን አለበት፡፡ ያለእምነት እግዚአብሄርን ደስ ማሰኘት አይቻልም፡፡ ከእግዚአብሄር ጋር የተሳካ ግንኙነት እንዲኖረን እምነት ወሳኝ ነው፡፡

ያለ እምነትም ደስ ማሰኘት አይቻልም፤ ወደ እግዚአብሔር የሚደርስ እግዚአብሔር እንዳለ ለሚፈልጉትም ዋጋ እንዲሰጥ ያምን ዘንድ ያስፈልገዋልና። ዕብራውያን 11፡6

እምነትን ደግሞ የምንለማመደው አሁን ነው፡፡

እምነት ረስተን ረስተን አስቸጋሪ ነገር ሲመጣ የምንመዘው መጠባበቂያ መሳሪያ አይደለም፡፡ እምነት በቀን ተቀን ህይወታችን የምንለማመደውና የምናዳብረው ነገር ነው፡፡

በሰውነት እንቅስቃሴ ልምምድ ሰውነታችንን እንደምናስለምደው ሁሉ ራስን ለመንፈሳዊነት ነገር ማስለመድ ጊዜንና የሚጠይቅ ነገር ነው፡፡ ማስለመድ የአንድ ቀን ስራ አይደለም፡፡ ይበልጥ ቶሎ ቶሎ እንደልምድ ካደረግነውና የህይወት ዘይቤያችን ከሆነ ይበልጥ ለከባድም ነገር ለመጠቀም እየቀለለ ይሄዳል፡፡

መፅሃፍ ቅዱስ ፈተና ሳይመጣ በፊት አስቀድመን ራሳችንን  ለፈተና በፀሎት መገንባት እንዳለብን ይናገራል፡፡

ወደ ፈተና እንዳትገቡ ትጉና ጸልዩ፤ መንፈስስ ተዘጋጅታለች ሥጋ ግን ደካማ ነው አለው። ማቴዎስ 26፡41

በህይወትም በመጀመሪያ በወጣትነታችን እግዚአብሄርን እንድንፈራና ህይወታችንን በእግዚአብሄር ሃሳብ እንድንገነባ መፅሃፍ ያስተምራል፡፡

የጭንቀት ቀን ሳይመጣ በጕብዝናህ ወራት ፈጣሪህን አስብ፤ ደስ አያሰኙም የምትላቸውም ዓመታት ሳይደርሱ፤መክብብ 12፡1

መፅሃፍ በክርስትና አዲስ የተወለዱ ህፃናት ለስጋና ለጠንካራ ምግብ ራሳቸውን ለማዳበር በታማኝነት ለወተት ታማኝ መሆን እንዳለባቸው ያስተምራል፡፡  

ጌታ ቸር መሆኑን ቀምሳችሁ እንደ ሆነ፥ ለመዳን በእርሱ እንድታድጉ አሁን እንደ ተወለዱ ሕፃናት ተንኰል የሌለበትን የቃልን ወተት ተመኙ። 1ኛ ጴጥሮስ 2፡2-3

እንዲሁም እምነት የምንለማመደው ከምናውቀው ከትንሹ ነገር ነው፡፡ በተረዳነው ከእግዚአብሄር ቃል የእምነትን እርምጃ መውሰድ እንጀምር፡፡ ይህ ቀላል ነገር ነው ከምንለው ጀምረን አግዚአብሄርን እንታዘዝ፡፡

ይህ የዛሬ ቀላል የእምነት እርምጃ ለነገው ከባዱ የእምነት እርምጃ መንፈሳዊ ጡንቻችንን ያሳድገዋል፡፡

  ይህን ፅሁፍ ለሌሎች ሼር   share ያድርጉ!



#ኢየሱስ #ጌታ #መሪነት #ቤተክርስትያን #አማርኛ #ስብከት #መዳን #መፅሃፍቅዱስ #ልብ #እምነት #ምሪት #ድምፅ #ጌታ #ሰላም #ደስታ #አቢይ #አቢይዋቁማ #አቢይዋቁማዲንሳ #እወጃ #መናገር #ፅናት #ትግስት #መሪ

No comments:

Post a Comment