Popular Posts

Thursday, September 29, 2016

እግዚአብሄር ሲመራ

እግዚአብሄር ለህዝቡ መናገር ህዝቡን መምራት ይወደል፡፡ እግዚአብሄር የሚናገረው ግን ብዙ ጊዜ እንደምንጠብቀው አይደለም፡፡ ሰዎችም እግዚአብሄር ተናገረኝ ሲሉ የሚመስለን በሚታይና ግልፅ በሆነ በእንቅስቃሴ በተደገፈ ሁኔታ እግዚአብሄር የሚናገር ነው፡፡
እውነት ነው እግዚአብሄር ሁሌ ለህዝቡ መናገር ስለሚወድ በእንደዚህ አይነት መልኩም ጭምር አንዳንዴ ይናገራል፡፡ በአብዛኛው ግን እግዚአብሄር እንደዚያ በደመናና በእሳት በውጫዊ ምልክት አይናገርም፡፡
ታዲያ እግዚአብሄር ለህዝቡ ሁል ጊዜ የሚናገር ከሆነና አብዛኛውን ጊዜ ደግሞ በግልፅና በሚታይ መልኩ ካልተናገረ እግዚአብሄር እንዴት ነው ብለን ልንጠይቅ እንችላለን፡፡
እግዚአብሄር አብዛኛውን ጊዜ የሚናገረን በልባችን ነው፡፡ ይህ በልባችን በዝምታ የምንሰማው ድምፅ በጣም ዝቅተኛ ከመሆኑ የተነሳ በልባችን ውስጥ ፈልገን ማግኘት ያለብን እኛው ራሳችን ነን፡፡
ይህን ድምፅ በልባችን ፈልገን ለማግኘት በራችንን መዝጋትና አእምሮዋችንንና ሌሎችን ድምፆች ሁሉ ዝም ማሰኘት ሊጠበቅብን ይችላል፡፡
ይህ ድምፅ በልባችን ሁሌ ያለ ሲሆን መጥቶ የሚሄድ አይነት ለተወሰነ ጊዜ ብቻ የሚሰማ ድንገተኛ ድምፅ አይደለም፡፡ ለምሳሌ ስለአንድ ነገር ስናስብ የእግዚአብሄር ፈቃድ ከሆነ የደስታና የምቾት ስሜትን የሚሰጠን ወይም ደግሞ የእግዚአብሄር ሃሳብ ካልሆነ የመኮስኮስ ፣ የመቆርቆርና ያለመመቸት ስሜትን በመስጠት የሚመራን ድምፅ ነው፡፡
በአንድ አካልም የተጠራችሁለት ደግሞ የክርስቶስ ሰላም በልባችሁ ይግዛ፤ ቆላስይስ 3፡15
ይህ በልባችን ውስጥ ፈልገን የምናገኘው ድምፅ ስለአንድ ነገር ስናስብ የእግዚአብሄርን የፈገግታ ፊትንና የእግዚአብሄርን የመኮሳተር ፊቱን በልባችን ፈልገን የምንለይበት ምሪት ነው፡፡
እግዚአብሔር አምላክ የሚናገረውን እሰማለሁ፤ ሰላምን ለሕዝቡና ለቅዱሳኑ ልባቸውንም ወደ እርሱ ለሚመልሱ ይናገራልና። መዝሙር 85፡8
ብዙ ጊዜ የእግዚአብሄርን ፈቃድ ለማወቅና ምሪቱን ለመከተል የምፈልገው በአእምሮዋችን ነው፡፡ እግዚአብሄር ግን የሚመራን በልባችን ነው፡፡ ስለአንድ ውሳኔ ስለሚያስፈልገው ነገር ስናስብ በልባችን ሰላምን ከሰጠን በአእምሮዋችን እንኳን ረብሻ ቢኖር መከተል ያለብን የልባችንን ምሪት ነው፡፡
ስለዚህ፥ እነሆ፥ አባብላታለሁ፥ ወደ ምድረ በዳም አመጣታለሁ፥ ለልብዋም እናገራለሁ። ሆሴዕ 2፡16
እግዚአብሄር ሁሌ ይናገራል፡፡ የእግዚአብሄርን ድምፅ ለመስማት ግን በጌታ ፊት በፀሎት ጊዜ መውሰድ ይጠይቃል፡፡ የእግዚአብሄርን ድምፅ ለመስማት በቃሉ ከባቢ ውስጥ መኖር ይጠይቃል፡፡
ይህን ፅሁፍ ለሌሎች ሼር share ያድርጉ!
ለተጨማሪ ፅሁፎች https://www.facebook.com/abiy.wakuma/notes
#ኢየሱስ #ጌታ #መሪነት #ቤተክርስትያን #አማርኛ #ስብከት #መዳን #መፅሃፍቅዱስ #ልብ #እምነት #ምሪት #ድምፅ #ጌታ #ሰላም #ደስታ #አቢይ #አቢይዋቁማ #አቢይዋቁማዲንሳ #እወጃ #መናገር #ፅናት #ትግስት #መሪ

No comments:

Post a Comment