Popular Posts

Tuesday, September 13, 2016

ፍቅር ሁሉን ያምናል

ፍቅር አስደናቂ ነው፡፡ በተለይ ፍቅር ሁሉን ያምናል የሚለውን ቃል ሳሰላስል ነበር ያመሸሁት፡፡ ይህን ቃል ሳሰላስል ጌታ የሰጠኝን መረዳት አብሬያችሁ ልካፈል ወደድኩ፡፡
ፍቅር ሁሉን ያምናል፡፡ 1ኛ ቆሮንጦስ 13፡7

ፍቅር ከሁኔታዎች ያለፈ የማየት ችሎታ አለው፡፡ ፍቅር በጊዜያዊ ሁኔታዎች ላይ አያተኩርም፡፡ከጊዜያዊ ሁኔታ ባለፈ በእግዚአብሔር እቅድ ላይ ስለሚያተኩር ፍቅር ሁሉን ያምናል፡፡
ፍቅር የጊዜያዊውን ብቻ ሳይሆን የሩቁንም ጭምር ያያል፡፡ ፍቅርን ለየት የሚያደርገው የሩቁን እንዲያውም ዘላለማዊውን ጭምር በርቀት ስለሚያይ ሁሉን ያምናል፡፡ ፍቅር በሰው ድካም ላይ አያተኩርም፡፡ ፍቅር ከሰው ድካም ባለፈ በሰው እምቅ ጉልበትና ችሎታ /Potential/ ላይ ያተኩራል፡፡ ፍቅር በድካም መካከል ብርታት የማየት ችሎታ አለው፡፡ ፍቅር ሁሉን ያምናል፡፡
ፍቅር ስለሰው መነሳት ስለሰው ማደግ ስለሰው መለወጥ ያምናል፡፡ ፍቅር እምነት አለው፡፡ ፍቅር ልቡ ሙሉ ነው፡፡ ፍቅር ሁሉን ያምናል፡፡ ፍቅር አይሆንም ብሎ ፍርሃትና ጥርጣሬ የለበትም፡፡ ፍቅር ሁሉን ያምናል፡፡ ፍፁም ፍቅር ፍርሃትን አውጥቶ እንደሚጥል ፍቅር ሁሉን ያምናል፡፡
ፍፁም ፍቅር ፍርሃትን አውጥቶ ይጥላል እንጂ በፍቅር ፍርሃት የለም። 1ኛ ዮሀንስ 4፡18
ፍቅር የማይለወጠውን የእግዚአብሔርን ምንጭ ያምናል፡፡ ፍቅር እግዚአብሔርን በማመን ሁሉን ያምናል፡፡ ፍቅር ማስተዋሉ በማይመረመር እግዚአብሄር ስለሚያምን ፍቅር ሁሉን ያምናል፡፡
እግዚአብሔር የዘላለም አምላክ፥ የምድርም ዳርቻ ፈጣሪ ነው፤ አይደክምም፥ አይታክትም፥ ማስተዋሉም አይመረመርም። ኢሳያስ 40፡28
ፍቅር እግዚአብሔር ሁኔታውን እንደተቆጣጠረው በማመን በሰዎች ያምናል፡፡ ፍቅር በእግዚአብሔር ሰዎችን የመምራት ችሎታ ላይ ስለሚደገፍና ስለሚተማመን ሁሉን ያምናል፡፡
ፍቅር እግዚአብሔር ሰዎችን እንደሚለውጥ በማመን በሰዎች መለወጥ ያምናል፡፡ ለእግዚአብሔር የሚሳነው ነገር የለምና። ሉቃስ 1:37
ፍቅር ለሚያምን ሁሉ እንደሚቻል ስለሚረዳ ሁሉን ያምናል፡፡ ሔ ፍቅር በእግዚአብሔር ሁሉን ቻይነት ስለሚያምን በሁሉ ያምናል፡፡ ኢዮብም መለሰ እግዚአብሔርንም እንዲህ አለው፦ሁሉን ታደርግ ዘንድ ቻይ እንደ ሆንህ፥ አሳብህም ይከለከል ዘንድ ከቶ እንደማይቻል አወቅሁ። ኢዮብ 42፡1-2
ፍቅር እግዚአብሔር ብርሃን ይሁን የማይለው ጨለማ እንደሌለ ስለሚረዳ ፍቅር ሁሉን ያምናል፡፡
ለተጨማሪ ፅሁፎች https://www.facebook.com/abiy.wakuma/notes
#እግዚአብሔር #አምላክ #ፍቅር #እምነት #ሰላም #ቃል #እረፍት #አምልኮ #ኢየሱስ #ጌታ #መሪነት #ቤተክርስትያን #አማርኛ #ስብከት #መዳን #መፅሃፍቅዱስ #አቢይ #አቢይዋቁማ #አቢይዋቁማዲንሳ

No comments:

Post a Comment