Popular Posts

Wednesday, August 31, 2016

ገርነት ሲተረጎም (Gentleness)

እግዚአብሄር ሰውን ሲፈጥረው በመልኩና በአምሳሉ ነው የፈጠረው፡፡ እግዚአብሄር ከሰው ከሚጠብቃቸው ባህሪያት አንዱ ገርነት ነው፡፡ ገርነት በክርስትና በጣም ተፈላጊ ባህሪ ሲሆን የእግዚአብሄርን ቃል በመቀበልና በመኖር የሚገነባ ወሳኝ ባህሪ ነው፡፡ ገር ሰው ሃይሉን ለክፋት ላለመጠቀም ኩሩ የሆነ የተገራ ሰው ነው፡፡
ገርነት በእግዚአብሄር ፊት ዋጋው እጅግ የከበረ ውበታችን ነው፡፡
ነገር ግን ውበታችሁ በእግዚአብሔር ፊት ዋጋው እጅግ የከበረ ገርና ጭምት መንፈስ ያለበት ምንጊዜም የማይጠፋ የውስጥ ሰውነት ውበት ይሁን፡፡ 1ኛ ጴጥሮስ 3፡4
ገርነትን በአንድ ቃል መተርጎም እጅግ አስቸጋሪ ቢሆንም ግን ተመሳሳይነት ባላቸው ቃላቶች ሊተረጎም ይችላል፡፡
ገር /ጀንትል/ ፡- ረጋ ያለ ፣ የማይጣላ ፣ የማይጨቃጨቅ ፣ ራስ ወዳድ ያልሆነ ፣ ጨዋ ፣ ለጥቅም የማይስገበገብ ፣ ዝግተኛ ፣ የዋህ ፣ ልከኛ ፣ አስተዋይ ፣ ሚዛናዊ ፣ በእግዚአብሄር የሚታመን ፣ በጎ ፣ አዛኝ ፣ የሚምር ፣ ትግስተኛ ፣ ርህሩህ ሰው ነው፡፡
  • ሰውን አክባሪ ፣ ሰውን አላግባብ ለመቆጣጠር የማይፈልግ ፣ የራሱን ጥቅም ብቻ የማያይ ፣ ሌላውን የሚረዳ ፣ አስተዋይ ፣ ሚዛናዊ
የጌታም ባሪያ ለሰው ሁሉ ገር ለማስተማርም የሚበቃ ለትዕግሥትም የሚጸና ሊሆን እንጂ ሊጣላ አይገባውም። 2ኛ ጢሞቴዎስ 2፥24
  • ለጥቅም የማይስገበገብ ፣ ኩሩ የሆነ ፣ የሚተው ፣ የራሱን ስሜት ብቻ የማይሰማ ፣ ሁሌ እኔ ብቻ ካላሸነፍኩ የማይል
የማይሰክር፥ የማይጨቃጨቅ ነገር ግን ገር የሆነ፥ የማይከራከር፥ ገንዘብን የማይወድ፥ 1ኛ ጢሞቴዎስ 3፥3
  • ሰው ከእግዚአብሄር የሆነ ጥበብ እንዳለው ወሳኙ መለኪያ ገርነትን በህይወቱ መታየቱ ነው፡፡
ላይኛይቱ ጥበብ ግን በመጀመሪያ ንጽሕት ናት፥ በኋላም ታራቂ፥ ገር፥ እሺ ባይ ምሕረትና በጎ ፍሬ የሞላባት፥ ጥርጥርና ግብዝነት የሌለባት ናት። ያዕቆብ 3፥17
  • የመሪነት አንዱ መመዘኛው በገርነት ህዝብን መምራት ነው፡፡
እኔም ራሴ ጳውሎስ፥ በእናንተ ዘንድ ፊት ለፊት ሳለሁ ትሑት የሆንሁ፥ ከእናንተ ግን ብርቅ የምደፍራችሁ፥ በክርስቶስ የዋህነትና ገርነት እመክራችኋለሁ፤ 2ኛ ቆሮንቶስ 10፥1
  • ከሰዎች ሁሉ ይልቁልንም ከማያምኑት ጋር ለመነጋገር ገርነት ወሳኝ ነው፡፡ ገርነትን ሁሉም ሰው ይረዳዋል፡፡
ዳሩ ግን ጌታን እርሱም ክርስቶስ በልባችሁ ቀድሱት። በእናንተ ስላለ ተስፋ ምክንያትን ለሚጠይቁአችሁ ሁሉ መልስ ለመስጠት ዘወትር የተዘጋጃችሁ ሁኑ፥ ነገር ግን በየዋህነትና በፍርሃት ይሁን። 1ኛ ጴጥሮስ 3፡15
  • ስለጌታ አዳኝነት የምንመሰክርበት አንደኛው ባህሪ ገርነት ነው፡፡ ጌታ እንዳዳነንና እንደለወጠን የምናሳይበት ባህሪ ገርነት ነው፡፡
ገርነታችሁ ለሰው ሁሉ ይታወቅ። ፊልጵስዩስ 4፥5
ይህን ፅሁፍ ለሌሎች ሼር share ማድረግ ቢወዱ

No comments:

Post a Comment