Popular Posts

Tuesday, June 28, 2016

ፈጣን ባለጠግነት

የታመነ ሰው እጅግ ይባረካል ባለጠጋ ለመሆን የሚቸኵል ግን ሳይቀጣ አይቀርም። ምሳሌ 28፡20
እግዚአብሄር በልጆቹ ብልፅግና መሳካትና መከናወን ደስ ይለዋል፡፡ እግዚአብሄር ይባርካል፡፡ እግዚአብሄር በማንም መባረክና ማግኘት ላይ ተቃውሞ የለውም፡፡ እንዲያውም መፅሃፍ ደስም እንዲለን ሁሉን አትርፎ በሚሰጠን በሕያው እግዚአብሔር እንድንመካ ያስተምረናል፡፡ 1ኛ ጢሞቴዎስ 6፡17 
የሰው ታማኝነት የሚታየው በአንድ ቀንና በአንድ ወር አይደለም፡፡ የሰው ታማኝነት የሚታየው በጊዜያት ውስጥ ነው፡፡ የታመነ ሰው በመታመን በቀጠለ መጠን ጥቂት በጥቂት እየጨመረ እየተባረከና እየበዛ ይሄዳል፡፡ 
እግዚአብሄር የራሱ እርምጃና ፍጥነት አለው፡፡ነገር ግን እግዚአብሄር በአንዴ አያሳድግም፡፡ 
ባለጠጋ ለመሆን መቸኮል ግን ችግር ነው፡፡ ፈጣኑ ባለጠግነት የእግዚአብሄር እጅ የለበትም፡፡ ፈጣኑ ባለጠግነት በፍፁም በንፅህና የሚመጣ አይደለም፡፡ ፈጣኑ ባለጠግነትና ከእግዚአብሄር ውጭ የሚመጣ ነው፡፡ 
ባለጠጋ ለመሆን የሚቸኩል ወይ ያጭበረብራል ወይ ይሰርቃል ወይ ይገድላል፡፡ ባለጠጋም ለመሆን ቸኩሎም ንፁህም መሆን አይቻልም፡፡ ባለጠጋ ለመሆን ቸኩሎም የእግዚአብሄርን በረከትንም ጠብቆም አይሆንም፡፡ 
ሰው ባለጠጋ ለመሆን ከቸኮለ የእግዚአብሄርን እርምጃ አልታገሰም ፡ እግዚአብሄርን በትግስት አልጠበቀም እንዲሁም የእግዚአብሄርን የበረከት መንገድ ትቶታል ማለት ነው፡፡ 
እግዚአብሄር የሚሰጠው ሃብት መሰረት ያለው ነው ሃዘንንም ከእርሱ ጋር አይጨምርም፡፡ 
የእግዚአብሔር በረከት ባለጠጋ ታደርጋለች፥ ኀዘንንም ከእርስዋ ጋር አይጨምርም። ምሳሌ 10፡22
በችኮላ የምትከማች ሃብት ግን የእግዚአብሄር እጅና ድጋፍ ስለሌለባት መሰረት እንደሌላት ቤት ነች፡፡ ተግንብታ ስታልቅ ከስርዋ ትናዳለች፡፡ 
በችኰላ የምትከማች ሀብት ትጐድላለች ጥቂት በጥቂት የተከማቸች ግን ትበዛለች። ምሳሌ 13፡11

No comments:

Post a Comment